“ለ24 ሰዓታት ሴት” (ምናባዊ ልብወለድ)፣ ተማሪዎቹስ? ግን እስከመቼ? | Ethio Teyim | Episode 19

ለአገሬ የህክምና ባለሞያዎች

በአስተዳደር በደል ምክንያት እጀ ሰባራ ለምትደረጉ፣
 
በsterilization መሳሪያ እጥረት ወይም በመብራት መቆራረጥ ምክንያት ጉልቻ ጥዳችሁ መሳሪያ ትቀቅሉ ዘንድ ለተፈረደባችሁ
 
ደም ለግሳችሁ ነፍስ ለማትረፍ ለምትተጉ
 
በላቦራቶሪ እና በዘመናዊ ዶክመንቴሽን ችግር ምክንያት የምርመራ ውጤት ለሚዘበራረቅባችሁ
 
የሀሰት ሪፖርት እንድትልኩ ለምትጠየቁ
 
በምንም ውስጥ ብዙ ተስፋ ለምትሰጡን፣ ስናያችሁ ብቻ ቀለል ለሚለን
 
ግራ ቢገባችሁ እና ምታደርጉት ብታጡ በእጃችሁ ዳብሳችሁ አይዞህ ለምትሉ
 
ችሎታ ሳያንሳችሁ፣ በስራ ቦታ አለመመቻቸት እና የህክምና ቁሳቁስ እጥረት የተነሳ አቅመ ቢስ ለምትሆኑ፣
 
አቅመ ቢሱን ካርድ አውጥታችሁ ለምታክሙ፣ መድኃኒት መግዣ ለምትሰጡ (ከፋርማሲ ጓንት ስትገዙም አይቼ አውቃለሁ)
 
በሙስና እና ብልሹ አሰራር ባለሀብቶች ባቆሙት የግል ሆስፒታል ውስጥ ይህን አርጉ ይህን አታርጉ ትንሽ ብላችሁ ለምትሰቃዩ
 
እኛ ሰው ለመጠየቅ ወይ ለህክምና ገብተን እስክንወጣ በሚጨንቀን የሚሸት ሆስፒታል/ጤና ጣቢያ ውስጥ ውላችሁ ለምታድሩ
 
በውሃና መብራት መቆራረጥ ምክንያት ትንፋሻችሁ አብሮ ለሚቆራረጥ
 
ቾክ እንደ መድኃኒት እየታሸገ እና ጊዜው ያለፈበት መድኃኒት በኮንትሮባንድ ይገባ ዘንድ በየእርከኑ ያሉ ባለጊዜዎች ተባብረው፣ የምታዙት መድኃኒት ታማሚውን ሳያሽል ሲቀር ለምትዘለፉ
 
በተፈጥሮ በሆነ ችግር በተከሰተ ጉዳይ ነፍስ ለማትረፍ ስትረባረቡ ባለጊዜ፣ ሽጉጥ ለሚመዝባችሁ (ከአንድም ሶስት ታሪክ አውቃለሁ። አንዱ በዐይኔ ያየሁት ነው) እልህ በማጋባት ወይም በማስደንበር ሊፈጥር ስለሚችለው ችግር ሳይጨነቅ፣ እያሳየ ሚያስፈራራም አለ።
 
በሽታው በየቅያሱ በሰው እጅ ለሚፈጠርባችሁ። (ጀሶ እና ሳጋቱራ ከመብላት ይጀምራል)
 
በተለይ ከመዲናዋ ከአዲስ አበባ ውጭ ለምትሰሩ፣ ሰርታችሁ ለምታውቁ!
 
ክብር ለእናንተ!
 
በበረሀ ላይ እንዳለ ዛፍ፥ ጥላና ተስፋ ናችሁ።
 
ሕይወት እንደነበር፣ ሕይወት እንደሚቀጥል ማሳያ ምልክቶች ናችሁ።
 
በተለይ የአሜሪካ ሀኪሞችን እና የህክምናውን ሁኔታ ባየሁ ቁጥር ልቤ ስለአገሬ ነዋሪ እና ስለ እናንተ ትደማለች። በእናንተ ሁኔታ ውስጥ ቢሆኑ፣ ግማሾቻቸውም survive ማድረግ ይችላሉ ብዬ አላስብም። የድሀ አገር ሰው መሆን ደግነቱ ጠንካራ ቆዳ ይሰጣል።
 
በምንም ውስጥ ሁሉንም ሆናችሁ የመኖራችሁ ነገርም እየደነቀኝ፣ ለእናንተ ያለኝ አክብሮት እና ፍቅር ይጨምራል። ልታከም የሄድኩበትን ጉዳይ ድኜ፣ ድብርት እና የጥፋተኝነት ስሜትን እታመማለሁ።
 
የእውቀት ችግር አለባችሁ እንዳይባል፣ ከማንም እንደምትሻሉ በየሰው አገሩ የወጡ የሞያ አጋሮቻችሁ ምስክር ናቸው። እንኳን ሀኪም፣ በየትኛውም ዘርፍ ላይ ኢትዮጵያዊያን ከማንም አያንስም። አንገት አያስደፋም።
 
ይህንን ስል የግል የጠባይ ችግር ያለባቸውን ሁሉ አካትቼ አይደለም። ዳሩ ግን መልካም ስርዓት ቢኖር ኖሮ፣ በወል ከመጠራት ይልቅ እነሱንም ተጠያቂ ማድረግ ይቻል ነበር።
 
አቅም ካገኘሁ ከሀኪም ጓደኞቼ ጋር በነበረኝ ውሎ የታዘብኩ የሰማኋቸውን፣ በአንድ ዓመት የሆስፒታል ሥራ (በፐብሊክ ኸልዝ) ቆይታዬ ያየሁ፣ የሰማሁ የታዘብኳቸውን፣ የማስታውሰቸውን ጥቂት ታሪኮች ለመጻፍ እሞክራለሁ።
 
ዛሬ ግን ይኽችን መጫሬ፥ አይዟችሁ፣ በርቱ፣ ሀሳቤ ከእናንተ ጋር ነው ለማለት ነው!
 
ዛሬ ድንግዝግዝ ቢሆንም፣ ሲነጋ ብርሃን ይሆናል።
 
ትግላችሁ ለሰፊው ሕዝብ የተሻለ ህክምና ለማስገኘት እና፣ ለዘርፉ ተገቢው ትኩረት እንዲሰጠው በማስቻል ትውልድ የሚያጣጥመውን መልካም ፍሬ ያፈራልና ዛሬ በብዙ ብትደክሙ፣ ብትዘለፉ፣ የሚዲያ ዘመቻ ቢደረግባችሁም አይዟችሁ!
 
መንግስት ሰብስቧችሁ እናንተን አንኳሶ እና ‘ስለህክምና ቱሪዝም የማታስቡ’ ብሎ ተሳልቆ፣ ወላድ እናት ደም የነካው ጨርቋ እንዲታጠብላት መብራት እና ውሃ በሌሉበት ከተማ፣ አዲስ አበባን አስውባለሁ፣ “ወንዞቿን አጥባለሁ” የሚል የ”ቂጥ ገልቦ ክንብንብ” ስላቅ ቢያደርግም፣ አይዟችሁ።
 
እኛንም አትፍረዱብን! ስንመጣ የምናየው የእናንተን ፊት ነውና ስላለው ቁም ስቅል፣ ስለ ህክምና ቁሳቁስ እጥረት፣ ስለሙስናው፣ ስለሕይወታችሁ ባንድረዳ ይቅር በሉን።
 
ጂጂ እና ቴዲ አፍሮ ከጋሪሰን ሃውክ ጋር ከተጫወቱት ሙዚቃ ላይ፣ በእነዚህ የጂጂ መስመሮች ላብቃ!
 
“በቀን በቀን የሚያኖረኝ
ተስፋ ሳልቆርጥ የሚያውለኝ
ዕምነቴ ነው ያለኝ ብርታት
ተሥፋ አልቆርጥም
ተሥፋ አትቁረጥ
አይፈራም አይፈራም
ጎበዝ አይፈራም
ተሥፋ አይቆርጥም”
 
ቴዲም እንዳለው
 
“ሀሳብ አይሆንም አይባልም
ከሀሰብኩት እደርሳለሁ”
 
ካሰባችሁት ደርሳችሁ ለወገን የህክምናውን ዘርፍ ለወገን እና ለአገር እንዲጠቅም ታሻሽሉት ዘንድ ተስፋ አደርጋለሁ!

የጉዞ ነገር…

images.jpgሁሉም የአፍሪካ አገራት ነዋሪዎች ወደኢትዮጵያ ለመግባት፣ በደረሱ ጊዜ ቪዛ ማግኘት የሚችሉበት አሠራር፣ ከኖቬምበር 10 ይጀምራል ተብሎ ነበር። (እንዴት ሆነ እንኳን “እንኳንስ ዘንቦብሽ እንዲሁም ጤዛ ነሽ” ይላሉ። የደህንነት ሁኔታው እንዲህ በሆነበት ጊዜ ጣጣው ብዙ ነው።
 
እሱን ባሉ በ20 ስንተኛ ቀኑ፥ አሁን ደግሞ ፓስፖርት ለማውጣት ቁም ስቅል ሆኗል ተብሏል። ወዳጆች ነገሩን ሲያወሩት ይኽን ያህል የተጋነነ ችግር አልመሰለኝም ነበር። ሰው እንዴት ፓስፖርት ለማውጣት መከራውን ያያል?
 
የሚሄድበት አገር ይጭነቀው እንጂ፣ እንዴት እና በምን ተለይቶ ይስተናገዳል?
 
ማን ነው አንቺ ቱሪስት ትመስያለሽ፣ አንቺ አትመስዪም ማለት የሚችለው?
 
በምንስ መስፈርት ነው?
 
ለምንስ እንደዚያ ይደረጋል?
 
በር ዘግቶ ስደት አስቀርተናል ለሚል ሪፖርት ነው?
 
ማንኛውም ሰው ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት አለው።
የሚሄድበት አገር አልቀበል ካላለው በስተቀርም፣ የፈለገበት ቦታ ሄዶ የመስራት እና የመኖር መብት አለው።
 
መብት የሆነውን ነፍገው፥ ምን ሸፍጥ እንዳሰቡ እንጃ… በጎን ለጎዳና ተዳዳሪዎች እና ለረጅም ጊዜ አዲስ አበባ ውስጥ ለኖሩ ሰዎች ጊዜያዊ መታወቂያ እንሰጣለን ይላሉ። ለምን አስፈለገ?
 
በዚህ በግርግር የቀበሌ ቤቶች ከድሃ ተነጥቀው ለባለጊዜ እየተሰጡ ነው ተብሎ በሚወራበት እና ምርጫና፣ ሕዝብ እና ቤት ቆጠራ በደረሰበት ጊዜ መታወቂያ መስጠቱ ለምን አስፈለገ?
 
መታወቂያው ቀርቶ ፓስፖርት ይሰጣቸውና እንደኢዮጵያዊ ይቆጠሩ።
 
#የጉድአገር

ስለሀሳብ ልዕልና ሲወራ…

ምርጫውን ፍትሀዊ እና ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ የተደረገው የቃል ተስፋ መልካም ነው። እግዚግዚአብሔር ፈቅዶ ምርጫው ነጻ ሆኖ ቢከናወን ግን፣ ኢህአዴግ በምን ቁመናው ሊቀጥል ይችላል? 🤔
 
በርግጥ “ከማያውቁት መልዐክ የሚያውቁት ሰይጣን” በሚል ብሂል የሚገብርላቸው ሊኖር ቢችልም ቅሉ፥ ለክፋታቸው ሲነዙት የኖሩት የብሄር አጀንዳ መልሶ እነሱኑ ሳይሰለቅጥ የሚመለስ በማይመስል መልኩ ተቀጣጥሏልና፥
 
“ምርጫው በነጻ እና ፍትሀዊ መንገድ እንዲደረግ ፈቃደኞች/ቁርጠኞች ነን” ማለታቸውን በራሱ፣ በሰላም እንደሚለቁ ቃል የገቡ ያህል እቆጥረዋለሁ።
 
(የሚነደው ግን፥ የነጻ እና ፍትሀዊ ምርጫ ወሬ እና ምኞት እንኳን ካለነሱ ፈቃድ የማይቻል የነበረ መሆኑ ነው። ይኽንንም ውለታ እንደዋሉ እንጂ መሆን እንዳለበት አይቆጥሩትም።)
 
ኢህአዴግ “ሀሳብ ሸጠን ነው የምናሸንፈው” ሲልና ስለሀሳብ ልዕልና ሲያወራ መስማት ይገርማል። እንደው ምናልባት በታምራት ደስታ (ነፍስ ይማር)
 
አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ
“አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ”
 
ብለው ይጀነጅኑን እንደው እንጂ ምን ቀራቸው?
 
አብረው ተባብረው ዘረፉ፣ ገረፉ፣ ደፈሩ፣ አባረሩ፣ ጣት ቀሰሩ፣ ጣት እንቆርጣለን ብለው ፎከሩ፣ ከፋፍለው አባሉ፣ ቀለም ጠልተው ቀለም ደፍተው፣ የቀለም ቀንድ ሰባብረው፣ ሕዝቡን በድንቁርና አጥረው አኖሩት፣ (ከርሞ ማመናቸውም ተመስገን ነው)፣ ምኑ ቅጡ ተሰፍሮ ተዘርዝሮ ያልቅና?
 
በተጭበረበረ ምርጫ ገነው፣ አሁንም በየመሀሉ በሊቀመንበራቸው በኩል “ተፎካካሪ” ያሉትን ይወቅሳሉ። ያስጠነቅቃሉ። ላይ ላዩን ገር ሆነው፣ ውስጥ ውስጡን አሁንም በሚዛን ሲቀመጡ እነሱ እንደሚሻሉ ያስባሉ። ያሳስባሉ።
 
በምርጫ ምክንያት ለተፈጠሩ ቀውሶች በሙሉ ዋናው ድርሻ ኢህአዴግ እንጂ ማን ሆኖ፣ አሁን “ወደኋላ ሄዶ ያለፈውን ማንሳት እና በትናንት መኖር አያስፈልግም” ካሉ በኋላ፣ በጨው መታጠብ ካልሆነ በቀር፣ መለስ ቀለስ እያሉ ሌላውን ለመውቀስ እና አበክሮ ለመውቀስስ ምን አቅም ያገኛሉ?
 
የኢህአዴግ ነገርማ
ያልጠፋነው፣
ከእግዚአብሔር ምህረት የተንሳ ነው”ን
እያስዘመረን የሚኖር ጉዳይ ነው!
 
እግዜር ቸር ቸሩን ያድርግልንማ!

ኢህአዴግ ጋዝ የነካው ምግብ…

ኢህአዴግ ጋዝ የነካው ምግብ ነው ስንል በምክንያት ነው። የጥቅም እና ዝርፊያ ተካፋይነቱን ሕወሃት የበላይ ሆኖ ቢሰፍርበትም፥ ትናንት ሁሉም በተመቸው እና ጊዜው በፈቀደለት ልክ ዘግኗል፣ አንገላቷል፣ በየፈርጁ እና በየደረጃውም፥ የግፉም የዝርፊያውም ተካፋይ ነበር። የሚደርሰው ወንጀል እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሁሉ እንዳይታወቅ በመሸፋፈን ረገድም ሁሉም አባል ይኽ ነው የማይባል ሚና ተጫውቷል። ምንም እንኳን በሕወሃት የበላይነት ቢዘወርም፥ የሰብአዊ መብት ጥሰቱን እና ንጹሐንን የማፈኑን ሥራም በድርጅት ደረጃ አቋም እና አተገባበር ይዘው ሲያደርጉት የነበረው ነውና፣ የጭንቀት ቀን ሲመጣ ጣት መቀሳሰሩ በኅሊና ዳኝነት ፊት የትም አያደርስም። ማናቸውም አሸባሪውን ድርጅት ሲያገለግሉ እንጂ፣ ገዳም አልነበሩም።

ሁሉም ደርሶ በድል አጥቢያ አርበኝነት ስሜት እና በለውጠኝነት ሽፋን ጣት ቀሳሪ ይሁን እንጂ፣ ለመዛኝ እና ለፈራጅነት የሚያበቃ ንጽህና ያለው ያን ያህል አይደለም። ምንም አያውቅም የሚባለው አባል እንኳን፣ ቢያንስ ዝም በማለት እና ንጹሐን ሲንገላቱ ባለመከላከል፣ ድሀ ሕዝብ ሲመዘበር የምዝበራው አበል ተካፋይ በመሆን እያመሰገነ እና፤ አባል ያልሆኑና ያገባኛል ያሉ ሰዎችን በጠላትነት እየፈረጀ ኖሯል። የኢትዮጵያ አምላክ ራቁት እሲያስቀር፣ የጊዜ ፈረስ እንዲህ በአፍጢም እስኪፈጠፍጥ ድረስ!

በርግጥ፥ አንድም ይሁን ሁለት፣ ያጠፋ ሰው መጠየቅ መጀመሩ አግባብ ነው። ሆኖም ግን፥ የሌላው ነውረኝነት አለመጋለጥ፣ የተጋለጡትን እና በህግ ለመጠየቅ መንገድ የተጀመረላቸውን ሰዎች ጉዳይ ስህተት አያደርገውም። ዛሬ ጊዜው ፈቅዷል፣ ትናንት አልፏል በሚል ቀመር፥ አብረው ሲፈተፍቱ፣ የሕዝብ ደም ሲገብሩ እና ነውሩን ሲጋርዱለት፣ በታማኝነት እና ቁርጠኝነት ሲያገለግሉት የነበሩትን ድርጅት “እኔ ከደሙ ንጹህ ነኝ” በሚል ጲላጦሳዊ ግብዝነት ሲነዛ ግን፥ አሁንም ህሊና ካለ ይፈርዳል።

እንደማሳያ፥ ሰሞኑን በድፍረታቸው እና አጋላጭነታቸው ተደንቀን፣ አፋችንን ከፍተን ሀቀኝነታቸውን የመሰከርንላቸውን አምባሳደር ሱለይማን ደደፎን የትዊተር ገጽ በጊዜ ወደ ኋላ ተመልሰን በመቃኘት ነገሬን ልቀጥል።

አቶ ሱለይማን ዛሬ ፓርቲአቸው ኦህዴድ የበላይ ባይሆን እና ሕወሃት ቢቀጥል ኖሮ፣ ሰጥ ለጥ ብለው የሚገዙ እንጂ “ግፍ አንገፈገፈኝ” ብለው የሚለቁ አይነት ነበሩ የሚያስችል የጀርባ ታሪክ እንዳላቸው የሚያሳይ ማስረጃ የለም። በርግጥ እሳቸው ብቻ ሳይሆኑ፣ ሌሎች አባላቶችም እንዲሁ ከመጣው ጋር ቀጥለው፣ በጥሎ ማለፍ ድርጅታቸውን እያሽሞነሞኑ ይቀጥሉ እንደነበር መገመትም ከባድ አይደለም። ድርጅታቸው ኢህአዴግን በታማኝነት ከማገልገል ባለፈ፥ ሲያደርግ የኖረውን ነገር በመሸፋፈን እና ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በማሳጣት የተጫወቱት ሚና ብዙ ነው።

በኦክቶበር 2013 የአፍሪካ አገራት በኢትዮጵያ መንግስት አዘጋጅነት፣ እነ ኡሁሩ ኬኒያታ የሰው ልጆች ላይ ወንጀል በመፈጸማቸው  በሚል መከሰሳቸውን ለመከላከል፥ በአዲስ አበባ አስቸኳይ ስብሰባ አድርገው ነበር። አጀንዳቸውም የዓለማቀፉን የወንጀል ፍርድቤት International Criminal Court (ICC) ለመቃወም ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በተባበሩት መንግስታት ስብሰባ ተገኝተውም ፍርድቤቱን መተቸታቸውን ተከትሎ፥ የአፍሪካ መሪዎችን ስብሰባ ጠርተው ነበር። ነገሩ “ነግ በእኔ”፤ “አፍንጫ ሲመታ አይን ያለቅሳል” ነበር። በተለይ ደግሞ የነገሩ ጠንሳሽ ኢትዮጵያ መሆኗ “ፈስ ያለበት ዝላይ አይችልም” ዓይነት ነበር።

ታዲያ ያንን ተከትሎ፥ ከሁለት ወይም ከሶስት ሳምንታት በኋላ በኦክቶበር 28 ቀን፥ አቶ ሱለይማን

I am skeptical on the very intention to create the ICC. Why doesn’t it open its eyes on the whole globe than giving excess attention to Africa?

በማለት ለአምባገነኖቹ የአፍሪካ መሪዎች መቆርቆራቸውን ገልጸው ነበር።

1

ኖቬምበር 15 ቀን 2013፥ የሳውዲ አረቢያ መንግስት በኢትዮጵያውያን ላይ እየደረሰ የነበረውን ስቃይ እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት በማውገዝ፣ ሰማያዊ ፓርቲ በሳውዲ አረቢያ ኤምባሲ ደጃፍ ላይ ለማካሄድ በጠራው የሰላማዊ ሰልፍ ላይ የወጡ ሰዎች፣ ላይ ፖሊስ የተቃውሞ ሰልፉን በመከልከል ሰዎችን ደብድቦ እና አስሮ ነበር።  ታዲያ በዚያን ቀን፥ አቶ ሱለይማን

Ethiopian Gov’t has allocated 50 million Birr to integrate Ethiopians deported from Saudi Arabia. But what do the opposition parties are doing? Ethiopian opposition parties are trying to benefit out of tears of Ethiopian migrants in Saudi Arabia as usual. Why?

ብለው በሁለት ትዊት ጽፈው ነበር።

2.jpg

በመጀመሪያ የኢትዮጵያ መንግስት ገንዘቡን የመደበው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ንብረት ላይ መሆኑን ዘንግተውት እንደልግስና ቆጥረውት ተመጻድቀው ነበር። ገንዘቡ በአግባቡ ይዋል አይዋልም አይታወቅም። ሆኖም ግን፥ በወቅቱ ለወገን በመቆርቆር የተጠራን ሰልፍ ተከትሎ፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን በጅምላ ለመፈረጅ እና፣ እንደ ኢህአዴግ አባልነታቸው “ተቃዋሚዎች በሕዝብ እንባ ለማትረፍ የሚሞክሩ ናቸው” ብሎ ስም ለመለጠፍ እና፣ “መንግስት ይህን ሲያደርግ፣ እነሱ ግን ምንም እንዳላደረጉ” ለማጉላት ዳክረው እንደነበር እናያለን።

20131115163925420734_20

(እንደፓርቲ ከአባላት ከሚያገኙት መዋጮ ላይ መቋቋሚያ እንዲሰጡ ጠብቀው ነበር ማለት ነው። እንደተቃዋሚ ፓርቲነታቸውም ለዜጎች ጥቃት መቆርቆራቸውንም አቃለዋል።) ከዚህ በላይ ኢህአዴን መጋረድ እና የሰብአዊ መብት ጥሰቱን መደገፍ ከየት ይመጣል?

እነ ወ/ሮ ሚሚ ስብሀቱ፣ አቤል ተስፋዬ እና መርከብ ነጋሽ ተሳትፈውበት በነበረ “የቀለም አብዮት” ዶክመንተሪ ማግስት፥ የዞን 9 ስድስት ጦማርያን እና 3 ጋዜጠኞች ወዳጆቻችን በአፕሪል 2014 መታሰራቸውን ተከትሎ፥ አቶ ሱለይማን፣ በሜይ 1 2014፥

Zone Niners are messangers of color revolution hired by neo-liberal masters. They are instructed to create violence ahead of next election. Press Freedom is not systematic invasion or campaign to change regime by color revolution. That is what the west are trying in Ethiopia.

ብለው ንጹሀን ላይ ጣታቸውን ቀስረው፣ እና የመንግስትን ጭቆና ለመሸፈን ሞክረው እንደነበርም እናስታውሳለን።

4.jpg

የመንግስትን የተጋነኑ “የኢንቨስትመንት” ወጪዎችን በተመለከተም፥ በዲሴምበር 3፣ 2014

Where will huge state investments lead Ethiopia? Obviously to growth

ብለው ጽፈው ነበር።

6

እንግዲህ ወደ እድገት ያመራናል ያሏቸውን ወጪዎች በተመለከተ ነው፣ አሁን ያላየ፣ ያልሰማ ሆነው በጻድቅ ምስክርነት የቆሙት። ምስክርነት መቆማቸውን መንቀፌ አይደለም፣ ነገር ግን ትህትና የቀላቀለ ቢሆንና፣ ሁላቸውም መነካካታቸውን የማይክድ መንፈስ ያረበበት አነጋገር ቢሆን የሚል የከሸፈ ጉጉት እንጂ።

በሌላ ማሳያ፥ የአሁኑ የጠቅላይ አቃቤ ህግ፣ የያኔው የፍትህ ሚንስትሩ አቶ ብርሃኑ ፀጋዬ፥ በ2011

ያለ ፍርድቤት ትዕዛዝ አይታሰርም። ያለፍርድቤት ውሳኔ አይቀጣም። በምርመራ ወቅት ድብደባ የለም። ግርፋት የለም። ሕገመንግስታችን ይከለክላል። እነዚህን ነገሮች ማለት ነው። ስለዚህ እንደዚህ ተደርጓል፣ እንደዚህ ተደርጓል ተብሎ አሉባልታ ካልሆነ በስተቀር በተጨባጭ እንደዚህ አይደረግም። በማረሚያ ቤት የሚገኙ፣ በምርመራ ላይ የሚገኙ፣ በፍርድቤትም የሚገኙ ማየትም፣ መጎብኘትም ይቻላል። እየተደረገም ነው። በውስጥም በውጭም ባሉት አካላት ነው። በዋናነት ለነዚህ አካላት አይደለም መንግስት እነዚህን ስራ የሚሰራው።

በዋናነት፥ ቅድም እንዳልኩት፣ ህገመንግስቱ ላይ የተቀመጡትን መብቶች የማስከበር፣ የማክበር ኃላፊነት የመንግስት ነው። ይሄም ህግ የወጣው፣ [የዜጎችን] መንግስት ሌት ተቀን እየሰራ ያለው፣ የዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስከበር ነው እንጂ ሌሎች ሶስተኛ ወገን የውጭ አካላትን ለማስደሰት፣ ወይ ደሞ ለማስቀየም አይደለም። ለዜጎች፣ የዜጎችን መብት ለማስጠበቅ፣ በአገራችን ውስጥ የዴሞክራሲ ስርዓት ስር እንዲሰድ ለማድረግ ነው እየተሰራ ያለው እንጂ፤ ለነዛ አካላት ተብሎ የሚሰራ ነገር አይደለምና፣ ጣልቃ የሚገባበት ነገርም አይኖርም።

ባሉበት አንደበታቸው፣ ባለፈው ሳምንት በቁጥጥር ሥር የዋሉ ሰዎችን አስመልክቶ የሰጡት መግለጫ ላይ፥ ይደርስ የነበረውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት የገለጹበትን መንገድ እናስታውሳለን። ቪዲዮውን እዚህ ይመልከቱ።

የበፊት ንግግራቸው መታወሱ ሲወራ፣ ወዲያውኑ ዋልታ የያኔውን ቪዲዮ ከድረ ገጹ ላይ ወዲያው ያነሳው ቢሆንም፣ ቀድመው ያወረዱት ሰዎች እየተቀባበሉት ተመልክተነዋል። (ዋልታስ ቪዲዮውን ማንሳቱ ምን ይባላል?)

እንግዲህ በደም የተጨማለቀ ስርዓትን በሀቀኝነት ማገልገል እና ሲደርስ የነበረውን ግፍ እና በደል ሁሉ፣ የሰብአዊ፣ የዴሞክራሲ እና የሕገመንግስት ሽፋን በመስጠት እንዳልነበሩ፥ አሁን ሌላው ላይ በሚናገሩት ነገር ህሊና ቢኖር ኖሮ አይሸመቅቅም ነበር ወይ?

ከላይም እንዳልኩት፥ ትናንት እንዲህ ተደርጎ ነበርና ዛሬ ዝም ይባል አይደለም። ቢያንስ ግን፥ ትናንት ተሳትፎ የነበራቸው፥ ከጋዜጠኛ እስከ ባለስልጣን፤ ከተራ አባል እስከ ፈላጭ ቆራጭ ድረስ፥ “ስላልተጋለጥን/ስለማንጋለጥ” በሚል ስሜት፥ ወይም በኖሩበት የአድርባይነት ስሜት፣ ነገሮችን ሲተርኩ፣ ፍጹም ከደሙ ንጹህ መስለው ለመታየት የሚያደርጉትን ነገር በልኩ ቢያደርጉት የሚል ነው። አሁንም ተጠያቂነት ድንበር አይኑረው!

እንግዲህ መመዘዝ የተጀመረው የሙስና እና የሰብዓዊ ጥቃት ክር የት ጋ እንደሚቆም በጉጉት እና በሌሎች በራሪ እንስሳዎች እናያለን! 😉

ዕድሜና ጤና ይስጠን እንጂ ከጊዜ ዳኝነት ማንም አያመልጥም!

ሰላም!

ስለ24 ዓመቷ ሌንሴ ኔሜ ሹመት

 

43371204_2460431533973313_7357390166161358848_n

የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስኪያጅ (CEO) ተደርጋ የተሾመችውን፣ የ24 ዓመቷን ሌሊሴ ኔሜ በተመለከተ መረጃውን ማጋራታችንን እና ነገሩን ማውገዛችንን ተከትሎ፣ በግራም በቀኝ ወዳጆች አስተያየት ሰጥተዋል።

 
ነገሩ ያስቆጣቸው በርካቶች የመኖራቸውን ያህል፣ በገራገርነት ተመልክተው “ከቻለች ምን ችግር አለው? ወጣት ወደ ሀላፊነት ሲመጣ ማበረታት ነው ያለብን” ዓይነት ሀሳብ የሰጡም አሉ።
 
ከዚያም አልፈው፣ ጽሁፉ ኦሮሞ ስለመሆኗ በማይገልጽበት ሁኔታ፥ “ገና ለገና ኦሮሞ ስለሆነች፤ የኦሮሞ ስም ስላላት” ብለው በልባቸው የሚያስቡትን (ምናልባትም እየሆነ ያለውን ስለሚታዘቡ) የተናገሩም አሉ።
 
ባረጀ ባፈጀ ማሸማቀቂያ “ኦሮሞፎቢያ” ያሉም አሉ። እንደዚህ እያልን እውነትን የምናፍንበት እና የምናሳቅቅበት ጊዜ ሳያልፍ አልቀረም። ስለኦሮሞነቷ ነው ብሎ ከማሰብ ይልቅ፣ “ከእሷ የተሻለ ለቦታው የሚበቃ ኦሮሞ ስለሌለ ነው ወይ?” ብሎ መጠየቅስ አይቀልም ነበረ? 
 
አሁን ማንሳት የፈለግኩት ግን ነገሩን በበጎ ተመልክተው “ምን ችግር አለው? ዋናው ብቃት ነው እንጂ ዕድሜ አይደለም። እስከቻለች ድረስ ትሁና።” ያሉትን ነው።
 
በመጀመሪያ እንደዚህ ያለ አገር አቀፍ ዋና ፕሮጀክት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሀላፊ (CEO)
መሆን ከልምድም ከእውቀትም አንጻር የሚጠይቀው ብዙ ነገር አለ። የነገሩን ትርጓሜ፣ የሚሰጠውን ሀላፊነት እና ዓለም ላይ እንዴት ነው የሚስራበት የሚለውን መፈተሽ ተገቢ ነው።
 
ብስለት እና አመራር ጋር ሲመጣ፣ ዕድሜ ቁጥር ብቻ አይደለም። የሚያሸክመው ልምድ፣ እውቀትና ብስለትም አለው። 24 ዓመት ተለዋዋጭ ፍላጎት እንኳን ጠርቶ ቦታ ይዣለሁ የማይልበት፣ ከራስ ጋር ተስማምተው የማይጨርሱበት ዕድሜ ነው።
 
እንደዚያ ባይሆን እንኳን፣ ከተመረቀች 2 ዓመት የሆናትን ወጣት ለዚህ ቦታ ለመሾም፣ መስፈርቱ እሷ የምታሟላውን ያህል ብቻ ሲሆን ነው። ካልሆነ ግን ቢያንስ ያስተማሯትም አሉና፣ የት ባሳየችው የአመራር ብቃት ነው ተመራጭ ሆና ለሹመት የምትበቃው?
 
(በርግጥ የሌንሴ የሹመት ሙስና እና ፖለቲካዊ አድልዎ የጀመረው ከዩኒቨርስቲ ከመመረቋ በተሰጣት ሹመት ነው። እንደዚያም ሆኖ እንኳን፣ ዩኒቨርስቲ ውስጥ የማስተማር ስራዋን ሳትተው፣ ዋና ስራ አስኪያጅነቱን ደርባ መስራት መቻሏም ሌላ አነጋጋሪ ጉዳይ ነው። ካልተሳሳትኩ፣ የስራ አጡ ቁጥር ባሻቀበበት አገራችን ላይ፣ ሁለት የመንግስት መስሪያ ቤት ተቀጥሮ መስራት በህግ የተከለከለ ነው። በዚያም ላይ በእንደዚህ ያለ ከፈተኛ የአመራር ስራ ላይ ያለ ሰው፣ መኪና የመንዳትን ስራ እንኳን ደርቦ እንዳይሰራ ጥንቃቄ ይደረግለታል።)
 
ቦታው የተሰጣት በሹመት ነው እንጂ፣ ማስታወቂያ ወጥቶ ሰዎች አመልክተው፣ በነጻ ተወዳድረው እና በገለልተኝነት ተመዝነው አለመሆኑ ነገሩን ከብቃት እና ከእውቀት ጋር እንዳናያይዘው ያደርገናል። ምናልባት እርሷ የትምህርት ቤት ጓደኞች መካከል (የዛሬ 2 ዓመት የተመረቁ) የመጀመሪያ ስራ እንኳን ይዘው የማያውቁ ይኖሩ ይሆናል። በጣም ችሎታ እያላቸው፣ በፓርቲ ተሳትፎ እና ትውውቅ የተነሳ ስራ አጥተው ባክነው የቀሩ ብዙ ሰዎች እንዳሉም ይታወቃል።
 
ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ “ከቻለችው ምን ችግር አለው? ዋናው መስራቷ ነው” የሚሉት አስተያየቶች ናቸው፣ ሌላ ትኩረቴን የሳቡት።
 
ታዲያ ትናንትና “የትግራይ የበላይነት ነገሰ” ያልነው ለምን ነበር?
 
አንድ መስሪያ ቤት ውስጥ ከጥበቃ እስከ ሀላፊ ድረስ ትግሬዎች ናቸው የሚቀጠሩት እና ቦታ ቦታ የያዙት የተባለው ለምንድን ነው?
 
ኮንዶሚነም ቤት እስከከፈሉ ድረስ ቢሰጣቸው ምን ችግር ነበረው?
 
የጥበቃ ሰራተኛው እስከጠበቀ ድረስ ትግሬ ሆነ ምን ሆነ ለምን ደነቀን?
 
የመከላከያ ሰራዊቱ ብሔር ስብጥር ለምን አሳሰበን?
 
የአውሮፕላን አስተናጋጇ እስካስተናገደች እና አውሮፕላኑ ስራ እስካላቆመ ድረስ፣ ትግሬ ሆነች ምን ሆነች ምን አገባን?
 
መርካቶ ንግዱ እስካልታጎለ ድረስ፣ ጉራጌዎችን አፈናቅለው በግብር እና በኮንትሮባንድ ደግፈው ትግሬዎችን ቢያስፋፉ ምን አስጨነቀን?
 
የተለያዩ ሀላፊነት ቦታዎች ላይ የተሾሙትስ አለመቻላቸው በምን ታወቀና ነው ትግሬ መሆናቸው ያስከፋን?
 
ታዲያ ድካማችን ሁሉ ለምን ነበር?
 
አገሪቱ ላይ ሁሉም ዜጋ እኩል ተጠቃሚ ይሁን ከሚል ቅንነት አይደለምን? ፍትህ እና ተጠያቂነት እንዲነግሱ፣ የዘመድ እና የካድሬ አሰራር እንዲወገድ አይደለምን?
 
“አዲስ ንጉስ እንጂ ለውጥ መቼ መጣ” የሚለው ሙዚቃ ትዝታ ይሁንልን! የትናንቱን የጠላነውን፣ በአዲስ ዛሬ ለመተካት አይደለም ተስፋ እና ጉጉቱ!
 
ኢፍትሀዊ አሰራር ይውደም!

ቤቲ እና ደሳለኝ፡ እንደወረደ! :)

የቤቲን እና የዶ/ር ደሳለኝን ቃለ መጠይቁን አየሁት። የተባለውን ያህል የተጋነነ ሆኖ ግን አላገኘሁትም። ደሳለኝ አለመዘጋጀቱ ያስታውቃል። መዘጋጀት ሲባል፣ ለቃለ መጠይቅ ሳይሆን፣ በአጠቃላይ እንደ ፓርቲ አመራር ራሱን በብዙ ነገሮች ውስጥ ማለማመድ እና ነጥሮ የወጣ ሀሳብ/መልስ የሚሆን ነገር ማዘጋጀት ነበረበት። አባላቱም እንዲሁ ማድረግ ነበረባቸው። ለከእንግዲውም መዘጋጀት አለባቸው።
 
በዋናነት ደሳለኝን የማይሆን ነገር ውስጥ የከተተው ጋሻው እና ክርስቲያን የተባሉ ስራ አስፈጻሚ አባላቶቹ ያደረጉትን ያልተገባ እና ያልበሰለ ንግግር ለማስተባበል እና “ማለት የፈለጉት” እያለ፣ ያላሉትን ሊልላቸው እና ያሉትን ሊያለባብስላቸው ባደረገው ጥረት ነው።
 
ከዚህ የምንማረው/የምንረዳው፣ አባላቱ (እንዲሁም ሌሎቻችን) ከፌስቡክ ወጣ እያሉ ወደ መጽሐፍት ገጾች አየት ማድረግ እንዳለባቸው ነው። እሱም ዐይኑን ያፈጠጠ፣ ጥርሱን ያገጠጠ ነገርን በይቅርታ ማለፍ ቢችል ተወዳጅነት እንደሚጨምርለት ከዶ/ር አብይ ኢህአዴግ መማር ይቻላል።
 
አብን ገና የሶስት ወር ጨቅላ ፓርቲ እንደመሆኑ መጠን ክፍተቶች ቢታዩ ብዙም ባያስደንቅም፣ ችኩል ችኩል እያሉ የፈጠሩትን ስህተት፣ “ሌላው ሰው ካለበት የመረዳት ችግር የተነሳ ነው እንጂ እኛ ልክ ነን” ማለት ወዳጅ እና ደጋፊ ያሳጣል እንጂ ሩቅ አያስኬድም። ከአሁኑ ያልተጀመረ ይቅርታ የመጠየቅ እና ራስን የማረም ባህልም፣ ውሎ አድሮ ስለመቀጠሉ መተማመኛ አይሰጥም።
 
ነገሮች በግልጽ ለክርክር እና ቅሬታ ክፍት በሆኑበት ቦታዎች/ሁኔታዎች “ስህተት ነበር። ይቅርታ። እንዳይደገም እንመክርበታለን።” ብሎ ማለፍ እየተቻለ፣ ባስረዳው ቁጥር የማይሆን ነገር ውስጥ ራሱን ከቷል። በዚህም፥ ከ27 እስከ 48 ደቂቃ ያለው ጊዜ በከንቱ እና ራሱን በማሳጣት የባከነ ነው። ልክ እንደዒድ በዓል መልካም ምኞት መግለጫው “ሌላን ሰው ካስከፋ ይቅርታ” ብሎ በሰላም እና በክብር አልፎት፣ ሀሳቦቹን ማስረጽ እና ሀሳብ ላይ ማውራት ይችል ነበር።
 
ደሳለኝ ምናልባትም ፓርቲውን (የፓርቲውን ስም) ለማስተዋወቅ ያህል ጥሩ እድል አገኘሁ ብሎ የሄደ ዓይነት ይመስላል። እሱ ደንገጥ ሲል እሷ በስሜታዊነት እየተናጠች ኮስተር ማለት መጀመሯ ነጻ ጋዜጠኛ የማያስብላት ነው። ጭራሽ ልትቆጣው ሁሉ የሚያምራት ቦታ አለ። ደካማ ጎን ያገኘች እየመሰላት፥ የልብ ልብ እየተሰማት፣ እንደ ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ፀጋዬ ለመሆን የፈለገችባቸው ቦታዎች ብዙ ናቸው።
 
እንደ ቃለመጠይቅ አድራጊነቷ እውነቱን እና ሀሳቡን መፈልፈልና ማውጣት ላይ እንጂ፣ የእሷን ሀሳብ ወይም መከላከያ እና ቅሬታ ማከል ላይ ማተኮሯ ለመደበኛ ቃለመጠይቅ የሚያስኬድ አይመስለኝም። ያም ሆኖ ግን፣ እንደፈለገች አድርጋ መጠየቅ መብቷ ነው። ሊያሰድባት የሚያደርስ ነገር የለም።
 
የተከፋ ሰው፥ ፕሮግራሞቿን አለመስማት፣ ወይም ደግሞ እሷ ጋ ቃለ መጠይቅ አልደረግም ብሎ ሊያምጽ ይችል ይሆናል፣ እንጂ “ሊቀመንበሬን ይህን ጠየቅሽብኝ፣ አጨናነቅሽብኝ” ብሎ የተሳደበ አባል ወይም ደጋፊ፥ እድሉን ቢያገኝ ልሰር ልግረፍ ማለት አያምረውም አይባልም እና “ሳይቃጠል፣ በቅጠል!” ነው መሆን ያለበት።
 
በየመሀሉ እየገባች በተነሳው ነገር ላይ ሁሉ ከኦሮሞ ጋር ማነጻጸሯም በአስፈላጊ ቦታ የሆነ አይደለም። ራሷንም ወደ ኦሮሞ ብሔር ያዘነበለች አድርጎ ያሳያታል።
 
ነገሬ ብላ ፓርቲውን ማሳጣት ላይ ወይም ራሷን እነደሀይለኛ ማስቆጠር ላይ ማተኮሯን የሚያሳይ፣ መሀል ላይ በቃለመጠይቁ ወቅት ያለተጠቀሰ እና ካለደሳለኝ እውቅና የተሰነቀረ የልማታዊ አርሶአደሮች ምስል አለ። በመንግስት የሚደገፈው የአማራ ክልል ቴሌቪዥን (መቼቱ አልተጠቀሰም) ለፕሮፖጋንዳ ያደረገውን ቃለ መጠይቅ እንደማስረጃ መሰንቀሯ ሳያንስ፣ እሱ ተመልክቶት ምላሽ እንዳይሰጥበት ማድረጓ የሙያን ስነምግባር ያጓደለ መሰለኝ።
 
ደሳለኝም ቢሆን “ውሻ በቀደደው ጅብ ይገባል” እንዲሉ፣ እሷ በጀመረችው ማነጻጸር ገብቶ ‘ፓርቲው የተቋቋመው፣ እና የምናደርገውን ሁሉ የምናደርገው ሌሎች ስላደረጉት ነው’ ዓይነት ገደምዳሜ ላይ እንድንደርስ የገፋፋን ይመስላል።
 
የአማራ ፓርቲ ሊቀመንበርነት፣ ፓርቲው ለመደራጀት ገፊ የሆነውን ምክንያት የስሙን ያህል፣ በጥናት እና ንባብ ተደግፎ አጣፍጦ ማስረዳት ይጠበቅበታል/ት ነበር። ቢያንስ ስለፕሮግራም ሲጠየቅ መደናገጥ የሚጠበቅ እና አስፈላጊ አልነበረም። እንጂ፣ ቢያንስ አማራ ኢትዮጵያን በመገንባት ሂደት ያበረከተውን ነገር ለመጥቀስ፣ ስነጥበቡን እና ኪነ ጥበቡን መጥቀስ ብቻውን ይበቃው ነበር።
የእድገት እና የስልጣኔ ጠቋሚ የሆኑትን የወሊድ ቁጥር መቀነስ እና ተያያዥ ዴሞግራፊክ ነገሮችን፣ እንደበደል ማቅረቡም ከምሁርነቱ አይጠበቅም። ከዚያ ይልቅ በቅርቡ እንኳን በአማራ ቴሌቪዥን ላይ የቀረቡትን የእስር ቤት አያያዝ ፕሮግራሞች ጠቅሶ መናገር ይችል ነበር።
 
የአካባቢውን የማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ሁኔታ፣ በጊዜ መዳርን ጨምሮ ሌሎች ልማዳዊ ድርጊቶች ያበረከቱትን አስተዋጾ፣ ት/ት እንዳይስፋፋ እና መሰረተ ልማቶች እንዳይከናወኑ በመደረጉ የደረሱትን ጥፋቶች፣ እንዲሁም ብዙ መውለድ ለመቀንጨር የሚያድርገውን አስተዋጽኦ እና ያም የሚያመጣውን የአእምሮ ውሱንነት ማሰብና፥ ጉዳዩን በተሻለ ማስረጃ ማቅረብ ነበረበት።
 
ወይ ደግሞ እንደ ኢህአዴግ/ብአዴን፥ ፓርቲው ዋና ዒላማ ያደረገው ገበሬውን ሆኖ፣ በአሉሽ አሉሽ እንፍሽፍሽ ማለፍ ፈልገው ይሆናል።
 
በዚህ የተነሳ፣ ማህበረሰቡ ሊደነቅበት በሚገባው ነገር ክስ ማጠናከሪያ አድርጎታል። (ልክ መስታወት ሲሰበር ይቆርጣል፤ ካዩበት ያሳያል እንደማለት ያለ፥ ነገሩን ከብዙ አንግል ማየት እና ትክክለኛ መከራከሪያ ማቅረብ ይቻላል። እኔ እንኳን ከሱ የተሻለ ይህንን ጉዳይ ማስረዳት የምችል ይመስለኛል።)
 
እሷም ጉዳዩ ላይ ንባብ ጠገብ ብትሆን ኖሮ፣ እዚህ ጋር ጥሩ ውይይት ያደርጉ ነበር። ባይሆን ግን የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ሪፖርቶች ላይ የአማራው ቁጥር አንሶ እንዲዘገብ የሚደረግበትን ምክንያት ማህበረ ፖለቲካዊ አድርጎ ማቅረብ እና ነጥብ ማስያዝ ይችል ነበር።
“በአብን ስም ያልተገባ ነገር የሚያደርጉ ስላሉ፣ ግለሰቦች ስለሚጽፉት ነገር ፓርቲው ሊወቀስ አይገባውም” ዓይነት ነገር ባለበት አንደበቱ፣ ስለእነ ግንቦት 7 ሲናገር ርግጠኛ ሆኖ “ደጋፊዎቻቸው” አባባሉም ከወገንተኝነት ያልጸዳ አቋም እንዳለው ነው የሚያሳየው።
 
ደግሞ በአብን ስም ለተደረጉ ስህተቶችስ፣ ፊት ለፊት ቀርቦ የእኛን ፓርቲ አይወክልም ብሎ ወዳጅንም ማረጋጋት፣ ጠላትንም ማስደንገጥ አይቻልም ወይ? ወይስ እንደ ኦነግ ሰው ተገድሎ፣ ሰው ተባሮ “አባላቶቼ አይደሉም። በስሜ ነው ይህን የሚያደርጉት።” ለማለት ነው የሚጠበቀው?
 
ሲመስለኝ፡
 
የአብን ነገር እንደ ትኩስ ሽልጦ “ጠዋት ተመርቶ፣ ከሰዓት መርካቶ” ዓይነት ይመስላል። ምናልባትም ዋና ግብ ያደረጉት ለመጪው ምርጫ መሳተፍ ነው።
 
የምር ለአማራው የሚቆረቆሩ ከሆነ ግን ከሕዝባዊ ስብሰባዎች እና ውይይቶች እኩል፣ ውስጣዊ ውይይቶች፣ የንባብ እና የርስበርስ ስልጠና፣ የመጽሐፍ ተዋውሶ ማንበብ ዝግጅቶችን ማድረግ ይኖርባቸዋል። ያድርጉ አያድርጉ ባላውቅም ከሚናገሯቸው እና ልዩነትን ከሚይዙባቸው ነገሮች ተነስተን፣ ክፍተት እንዳለ በግልጽ መናገር ይቻላል።
ነገሩን ጠቅለል ስናደርገው፡
 
ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ አብንን ሳይወክል፥ ስለአብንም ሆነ አማራ መደራጀት ቢጠየቅ ከዚህ የተሻለ ቃለመጠይቅ ማድረግ ይችል ነበር ብዬ አስባለሁ! ይህም የሚሆነው ከእርጋታ እና ነገሩ ላይ ከመብሰል እንጂ፣ ከግል አቅም አይደለም። ዶ/ር ደሳለኝ እርጋታውን እና ቅንነቱን አሳይቷል።
አብን እንደሶስት ወር ዕድሜው በጣም ጥሩ እየሰራ ነው! እንደ አማራ ሕዝብ ግን ገና ነው! ለሰፊው እና ስልጡኑ አማራ ሕዝብ አብን ይጠበዋል።
 
ባልተያያዘ ወሬ ደግሞ፡
 
እሱ “አብን ለሕብረ ብሔራዊ ድርጅቶች ስጋት ነው” ያላትን ወስጄ፥ ሕብረ ብሔራዊው ግንቦት 7፣ ለአብን ስጋት እንዳይሆን እንደሚፈሩ፤ አባላቱም በዚህም ስጋት የተነሳ ግንቦት7ን ማጥላላት ላይ እንደተጠመዱ ብነግረው አልጠላም።
 
በቅንነት ተደራጁ! የተደራጃችሁም በቅንነት ተራመዱ! በርቱ!
ሰላም!

እንደወረደ! ;)

የቤቲን እና የዶ/ር ደሳለኝን ቃለ መጠይቁን አየሁት። የተባለውን ያህል የተጋነነ ሆኖ ግን አላገኘሁትም። ደሳለኝ አለመዘጋጀቱ ያስታውቃል። መዘጋጀት ሲባል፣ ለቃለ መጠይቅ ሳይሆን፣ በአጠቃላይ እንደ ፓርቲ አመራር ራሱን በብዙ ነገሮች ውስጥ ማለማመድ እና ነጥሮ የወጣ ሀሳብ/መልስ የሚሆን ነገር ማዘጋጀት ነበረበት። አባላቱም እንዲሁ ማድረግ ነበረባቸው። ለከእንግዲውም መዘጋጀት አለባቸው።
 
በዋናነት ደሳለኝን የማይሆን ነገር ውስጥ የከተተው ጋሻው እና ክርስቲያን የተባሉ ስራ አስፈጻሚ አባላቶቹ ያደረጉትን ያልተገባ እና ያልበሰለ ንግግር ለማስተባበል እና “ማለት የፈለጉት” እያለ፣ ያላሉትን ሊልላቸው እና ያሉትን ሊያለባብስላቸው ባደረገው ጥረት ነው።
 
ከዚህ የምንማረው/የምንረዳው፣ አባላቱ (እንዲሁም ሌሎቻችን) ከፌስቡክ ወጣ እያሉ ወደ መጽሐፍት ገጾች አየት ማድረግ እንዳለባቸው ነው። እሱም ዐይኑን ያፈጠጠ፣ ጥርሱን ያገጠጠ ነገርን በይቅርታ ማለፍ ቢችል ተወዳጅነት እንደሚጨምርለት ከዶ/ር አብይ ኢህአዴግ መማር ይቻላል።
 
አብን ገና የሶስት ወር ጨቅላ ፓርቲ እንደመሆኑ መጠን ክፍተቶች ቢታዩ ብዙም ባያስደንቅም፣ ችኩል ችኩል እያሉ የፈጠሩትን ስህተት፣ “ሌላው ሰው ካለበት የመረዳት ችግር የተነሳ ነው እንጂ እኛ ልክ ነን” ማለት ወዳጅ እና ደጋፊ ያሳጣል እንጂ ሩቅ አያስኬድም። ከአሁኑ ያልተጀመረ ይቅርታ የመጠየቅ እና ራስን የማረም ባህልም፣ ውሎ አድሮ ስለመቀጠሉ መተማመኛ አይሰጥም።
 
ነገሮች በግልጽ ለክርክር እና ቅሬታ ክፍት በሆኑበት ቦታዎች/ሁኔታዎች “ስህተት ነበር። ይቅርታ። እንዳይደገም እንመክርበታለን።” ብሎ ማለፍ እየተቻለ፣ ባስረዳው ቁጥር የማይሆን ነገር ውስጥ ራሱን ከቷል። በዚህም፥ ከ27 እስከ 48 ደቂቃ ያለው ጊዜ በከንቱ እና ራሱን በማሳጣት የባከነ ነው። ልክ እንደዒድ በዓል መልካም ምኞት መግለጫው “ሌላን ሰው ካስከፋ ይቅርታ” ብሎ በሰላም እና በክብር አልፎት፣ ሀሳቦቹን ማስረጽ እና ሀሳብ ላይ ማውራት ይችል ነበር።
 
ደሳለኝ ምናልባትም ፓርቲውን (የፓርቲውን ስም) ለማስተዋወቅ ያህል ጥሩ እድል አገኘሁ ብሎ የሄደ ዓይነት ይመስላል። እሱ ደንገጥ ሲል እሷ በስሜታዊነት እየተናጠች ኮስተር ማለት መጀመሯ ነጻ ጋዜጠኛ የማያስብላት ነው። ጭራሽ ልትቆጣው ሁሉ የሚያምራት ቦታ አለ። ደካማ ጎን ያገኘች እየመሰላት፥ የልብ ልብ እየተሰማት፣ እንደ ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ፀጋዬ ለመሆን የፈለገችባቸው ቦታዎች ብዙ ናቸው።
 
እንደ ቃለመጠይቅ አድራጊነቷ እውነቱን እና ሀሳቡን መፈልፈልና ማውጣት ላይ እንጂ፣ የእሷን ሀሳብ ወይም መከላከያ እና ቅሬታ ማከል ላይ ማተኮሯ ለመደበኛ ቃለመጠይቅ የሚያስኬድ አይመስለኝም። ያም ሆኖ ግን፣ እንደፈለገች አድርጋ መጠየቅ መብቷ ነው። ሊያሰድባት የሚያደርስ ነገር የለም።
 
የተከፋ ሰው፥ ፕሮግራሞቿን አለመስማት፣ ወይም ደግሞ እሷ ጋ ቃለ መጠይቅ አልደረግም ብሎ ሊያምጽ ይችል ይሆናል፣ እንጂ “ሊቀመንበሬን ይህን ጠየቅሽብኝ፣ አጨናነቅሽብኝ” ብሎ የተሳደበ አባል ወይም ደጋፊ፥ እድሉን ቢያገኝ ልሰር ልግረፍ ማለት አያምረውም አይባልም እና “ሳይቃጠል፣ በቅጠል!” ነው መሆን ያለበት።
 
በየመሀሉ እየገባች በተነሳው ነገር ላይ ሁሉ ከኦሮሞ ጋር ማነጻጸሯም በአስፈላጊ ቦታ የሆነ አይደለም። ራሷንም ወደ ኦሮሞ ብሔር ያዘነበለች አድርጎ ያሳያታል።
 
ነገሬ ብላ ፓርቲውን ማሳጣት ላይ ወይም ራሷን እነደሀይለኛ ማስቆጠር ላይ ማተኮሯን የሚያሳይ፣ መሀል ላይ በቃለመጠይቁ ወቅት ያለተጠቀሰ እና ካለደሳለኝ እውቅና የተሰነቀረ የልማታዊ አርሶአደሮች ምስል አለ። በመንግስት የሚደገፈው የአማራ ክልል ቴሌቪዥን (መቼቱ አልተጠቀሰም) ለፕሮፖጋንዳ ያደረገውን ቃለ መጠይቅ እንደማስረጃ መሰንቀሯ ሳያንስ፣ እሱ ተመልክቶት ምላሽ እንዳይሰጥበት ማድረጓ የሙያን ስነምግባር ያጓደለ መሰለኝ።
 
ደሳለኝም ቢሆን “ውሻ በቀደደው ጅብ ይገባል” እንዲሉ፣ እሷ በጀመረችው ማነጻጸር ገብቶ ‘ፓርቲው የተቋቋመው፣ እና የምናደርገውን ሁሉ የምናደርገው ሌሎች ስላደረጉት ነው’ ዓይነት ገደምዳሜ ላይ እንድንደርስ የገፋፋን ይመስላል።
 
የአማራ ፓርቲ ሊቀመንበርነት፣ ፓርቲው ለመደራጀት ገፊ የሆነውን ምክንያት የስሙን ያህል፣ በጥናት እና ንባብ ተደግፎ አጣፍጦ ማስረዳት ይጠበቅበታል/ት ነበር። ቢያንስ ስለፕሮግራም ሲጠየቅ መደናገጥ የሚጠበቅ እና አስፈላጊ አልነበረም። እንጂ፣ ቢያንስ አማራ ኢትዮጵያን በመገንባት ሂደት ያበረከተውን ነገር ለመጥቀስ፣ ስነጥበቡን እና ኪነ ጥበቡን መጥቀስ ብቻውን ይበቃው ነበር።
የእድገት እና የስልጣኔ ጠቋሚ የሆኑትን የወሊድ ቁጥር መቀነስ እና ተያያዥ ዴሞግራፊክ ነገሮችን፣ እንደበደል ማቅረቡም ከምሁርነቱ አይጠበቅም። ከዚያ ይልቅ በቅርቡ እንኳን በአማራ ቴሌቪዥን ላይ የቀረቡትን የእስር ቤት አያያዝ ፕሮግራሞች ጠቅሶ መናገር ይችል ነበር።
 
የአካባቢውን የማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ሁኔታ፣ በጊዜ መዳርን ጨምሮ ሌሎች ልማዳዊ ድርጊቶች ያበረከቱትን አስተዋጾ፣ ት/ት እንዳይስፋፋ እና መሰረተ ልማቶች እንዳይከናወኑ በመደረጉ የደረሱትን ጥፋቶች፣ እንዲሁም ብዙ መውለድ ለመቀንጨር የሚያድርገውን አስተዋጽኦ እና ያም የሚያመጣውን የአእምሮ ውሱንነት ማሰብና፥ ጉዳዩን በተሻለ ማስረጃ ማቅረብ ነበረበት።
 
ወይ ደግሞ እንደ ኢህአዴግ/ብአዴን፥ ፓርቲው ዋና ዒላማ ያደረገው ገበሬውን ሆኖ፣ በአሉሽ አሉሽ እንፍሽፍሽ ማለፍ ፈልገው ይሆናል።
 
በዚህ የተነሳ፣ ማህበረሰቡ ሊደነቅበት በሚገባው ነገር ክስ ማጠናከሪያ አድርጎታል። (ልክ መስታወት ሲሰበር ይቆርጣል፤ ካዩበት ያሳያል እንደማለት ያለ፥ ነገሩን ከብዙ አንግል ማየት እና ትክክለኛ መከራከሪያ ማቅረብ ይቻላል። እኔ እንኳን ከሱ የተሻለ ይህንን ጉዳይ ማስረዳት የምችል ይመስለኛል።)
 
እሷም ጉዳዩ ላይ ንባብ ጠገብ ብትሆን ኖሮ፣ እዚህ ጋር ጥሩ ውይይት ያደርጉ ነበር። ባይሆን ግን የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ሪፖርቶች ላይ የአማራው ቁጥር አንሶ እንዲዘገብ የሚደረግበትን ምክንያት ማህበረ ፖለቲካዊ አድርጎ ማቅረብ እና ነጥብ ማስያዝ ይችል ነበር።
“በአብን ስም ያልተገባ ነገር የሚያደርጉ ስላሉ፣ ግለሰቦች ስለሚጽፉት ነገር ፓርቲው ሊወቀስ አይገባውም” ዓይነት ነገር ባለበት አንደበቱ፣ ስለእነ ግንቦት 7 ሲናገር ርግጠኛ ሆኖ “ደጋፊዎቻቸው” አባባሉም ከወገንተኝነት ያልጸዳ አቋም እንዳለው ነው የሚያሳየው።
 
ደግሞ በአብን ስም ለተደረጉ ስህተቶችስ፣ ፊት ለፊት ቀርቦ የእኛን ፓርቲ አይወክልም ብሎ ወዳጅንም ማረጋጋት፣ ጠላትንም ማስደንገጥ አይቻልም ወይ? ወይስ እንደ ኦነግ ሰው ተገድሎ፣ ሰው ተባሮ “አባላቶቼ አይደሉም። በስሜ ነው ይህን የሚያደርጉት።” ለማለት ነው የሚጠበቀው?
 
ሲመስለኝ፡
 
የአብን ነገር እንደ ትኩስ ሽልጦ “ጠዋት ተመርቶ፣ ከሰዓት መርካቶ” ዓይነት ይመስላል። ምናልባትም ዋና ግብ ያደረጉት ለመጪው ምርጫ መሳተፍ ነው።
 
የምር ለአማራው የሚቆረቆሩ ከሆነ ግን ከሕዝባዊ ስብሰባዎች እና ውይይቶች እኩል፣ ውስጣዊ ውይይቶች፣ የንባብ እና የርስበርስ ስልጠና፣ የመጽሐፍ ተዋውሶ ማንበብ ዝግጅቶችን ማድረግ ይኖርባቸዋል። ያድርጉ አያድርጉ ባላውቅም ከሚናገሯቸው እና ልዩነትን ከሚይዙባቸው ነገሮች ተነስተን፣ ክፍተት እንዳለ በግልጽ መናገር ይቻላል።
ነገሩን ጠቅለል ስናደርገው፡
 
ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ አብንን ሳይወክል፥ ስለአብንም ሆነ አማራ መደራጀት ቢጠየቅ ከዚህ የተሻለ ቃለመጠይቅ ማድረግ ይችል ነበር ብዬ አስባለሁ! ይህም የሚሆነው ከእርጋታ እና ነገሩ ላይ ከመብሰል እንጂ፣ ከግል አቅም አይደለም። ዶ/ር ደሳለኝ እርጋታውን እና ቅንነቱን አሳይቷል።
አብን እንደሶስት ወር ዕድሜው በጣም ጥሩ እየሰራ ነው! እንደ አማራ ሕዝብ ግን ገና ነው! ለሰፊው እና ስልጡኑ አማራ ሕዝብ አብን ይጠበዋል።
 
ባልተያያዘ ወሬ ደግሞ፡
 
እሱ “አብን ለሕብረ ብሔራዊ ድርጅቶች ስጋት ነው” ያላትን ወስጄ፥ ሕብረ ብሔራዊው ግንቦት 7፣ ለአብን ስጋት እንዳይሆን እንደሚፈሩ፤ አባላቱም በዚህም ስጋት የተነሳ ግንቦት7ን ማጥላላት ላይ እንደተጠመዱ ብነግረው አልጠላም።
 
በቅንነት ተደራጁ! የተደራጃችሁም በቅንነት ተራመዱ! በርቱ!
ሰላም!