የጉዞ ነገር…

images.jpgሁሉም የአፍሪካ አገራት ነዋሪዎች ወደኢትዮጵያ ለመግባት፣ በደረሱ ጊዜ ቪዛ ማግኘት የሚችሉበት አሠራር፣ ከኖቬምበር 10 ይጀምራል ተብሎ ነበር። (እንዴት ሆነ እንኳን “እንኳንስ ዘንቦብሽ እንዲሁም ጤዛ ነሽ” ይላሉ። የደህንነት ሁኔታው እንዲህ በሆነበት ጊዜ ጣጣው ብዙ ነው።
 
እሱን ባሉ በ20 ስንተኛ ቀኑ፥ አሁን ደግሞ ፓስፖርት ለማውጣት ቁም ስቅል ሆኗል ተብሏል። ወዳጆች ነገሩን ሲያወሩት ይኽን ያህል የተጋነነ ችግር አልመሰለኝም ነበር። ሰው እንዴት ፓስፖርት ለማውጣት መከራውን ያያል?
 
የሚሄድበት አገር ይጭነቀው እንጂ፣ እንዴት እና በምን ተለይቶ ይስተናገዳል?
 
ማን ነው አንቺ ቱሪስት ትመስያለሽ፣ አንቺ አትመስዪም ማለት የሚችለው?
 
በምንስ መስፈርት ነው?
 
ለምንስ እንደዚያ ይደረጋል?
 
በር ዘግቶ ስደት አስቀርተናል ለሚል ሪፖርት ነው?
 
ማንኛውም ሰው ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት አለው።
የሚሄድበት አገር አልቀበል ካላለው በስተቀርም፣ የፈለገበት ቦታ ሄዶ የመስራት እና የመኖር መብት አለው።
 
መብት የሆነውን ነፍገው፥ ምን ሸፍጥ እንዳሰቡ እንጃ… በጎን ለጎዳና ተዳዳሪዎች እና ለረጅም ጊዜ አዲስ አበባ ውስጥ ለኖሩ ሰዎች ጊዜያዊ መታወቂያ እንሰጣለን ይላሉ። ለምን አስፈለገ?
 
በዚህ በግርግር የቀበሌ ቤቶች ከድሃ ተነጥቀው ለባለጊዜ እየተሰጡ ነው ተብሎ በሚወራበት እና ምርጫና፣ ሕዝብ እና ቤት ቆጠራ በደረሰበት ጊዜ መታወቂያ መስጠቱ ለምን አስፈለገ?
 
መታወቂያው ቀርቶ ፓስፖርት ይሰጣቸውና እንደኢዮጵያዊ ይቆጠሩ።
 
#የጉድአገር

ስለሀሳብ ልዕልና ሲወራ…

ምርጫውን ፍትሀዊ እና ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ የተደረገው የቃል ተስፋ መልካም ነው። እግዚግዚአብሔር ፈቅዶ ምርጫው ነጻ ሆኖ ቢከናወን ግን፣ ኢህአዴግ በምን ቁመናው ሊቀጥል ይችላል? 🤔
 
በርግጥ “ከማያውቁት መልዐክ የሚያውቁት ሰይጣን” በሚል ብሂል የሚገብርላቸው ሊኖር ቢችልም ቅሉ፥ ለክፋታቸው ሲነዙት የኖሩት የብሄር አጀንዳ መልሶ እነሱኑ ሳይሰለቅጥ የሚመለስ በማይመስል መልኩ ተቀጣጥሏልና፥
 
“ምርጫው በነጻ እና ፍትሀዊ መንገድ እንዲደረግ ፈቃደኞች/ቁርጠኞች ነን” ማለታቸውን በራሱ፣ በሰላም እንደሚለቁ ቃል የገቡ ያህል እቆጥረዋለሁ።
 
(የሚነደው ግን፥ የነጻ እና ፍትሀዊ ምርጫ ወሬ እና ምኞት እንኳን ካለነሱ ፈቃድ የማይቻል የነበረ መሆኑ ነው። ይኽንንም ውለታ እንደዋሉ እንጂ መሆን እንዳለበት አይቆጥሩትም።)
 
ኢህአዴግ “ሀሳብ ሸጠን ነው የምናሸንፈው” ሲልና ስለሀሳብ ልዕልና ሲያወራ መስማት ይገርማል። እንደው ምናልባት በታምራት ደስታ (ነፍስ ይማር)
 
አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ
“አንድ ዕድል ሰጥተሽኝ ልካስሽ ደግሜ፣
ያውም አገልጋይሽ ታማኝ ባሪያሽ ሆኜ”
 
ብለው ይጀነጅኑን እንደው እንጂ ምን ቀራቸው?
 
አብረው ተባብረው ዘረፉ፣ ገረፉ፣ ደፈሩ፣ አባረሩ፣ ጣት ቀሰሩ፣ ጣት እንቆርጣለን ብለው ፎከሩ፣ ከፋፍለው አባሉ፣ ቀለም ጠልተው ቀለም ደፍተው፣ የቀለም ቀንድ ሰባብረው፣ ሕዝቡን በድንቁርና አጥረው አኖሩት፣ (ከርሞ ማመናቸውም ተመስገን ነው)፣ ምኑ ቅጡ ተሰፍሮ ተዘርዝሮ ያልቅና?
 
በተጭበረበረ ምርጫ ገነው፣ አሁንም በየመሀሉ በሊቀመንበራቸው በኩል “ተፎካካሪ” ያሉትን ይወቅሳሉ። ያስጠነቅቃሉ። ላይ ላዩን ገር ሆነው፣ ውስጥ ውስጡን አሁንም በሚዛን ሲቀመጡ እነሱ እንደሚሻሉ ያስባሉ። ያሳስባሉ።
 
በምርጫ ምክንያት ለተፈጠሩ ቀውሶች በሙሉ ዋናው ድርሻ ኢህአዴግ እንጂ ማን ሆኖ፣ አሁን “ወደኋላ ሄዶ ያለፈውን ማንሳት እና በትናንት መኖር አያስፈልግም” ካሉ በኋላ፣ በጨው መታጠብ ካልሆነ በቀር፣ መለስ ቀለስ እያሉ ሌላውን ለመውቀስ እና አበክሮ ለመውቀስስ ምን አቅም ያገኛሉ?
 
የኢህአዴግ ነገርማ
ያልጠፋነው፣
ከእግዚአብሔር ምህረት የተንሳ ነው”ን
እያስዘመረን የሚኖር ጉዳይ ነው!
 
እግዜር ቸር ቸሩን ያድርግልንማ!