“ለ24 ሰዓታት ሴት” (ምናባዊ ልብወለድ)፣ ተማሪዎቹስ? ግን እስከመቼ? | Ethio Teyim | Episode 19

ለአገሬ የህክምና ባለሞያዎች

በአስተዳደር በደል ምክንያት እጀ ሰባራ ለምትደረጉ፣
 
በsterilization መሳሪያ እጥረት ወይም በመብራት መቆራረጥ ምክንያት ጉልቻ ጥዳችሁ መሳሪያ ትቀቅሉ ዘንድ ለተፈረደባችሁ
 
ደም ለግሳችሁ ነፍስ ለማትረፍ ለምትተጉ
 
በላቦራቶሪ እና በዘመናዊ ዶክመንቴሽን ችግር ምክንያት የምርመራ ውጤት ለሚዘበራረቅባችሁ
 
የሀሰት ሪፖርት እንድትልኩ ለምትጠየቁ
 
በምንም ውስጥ ብዙ ተስፋ ለምትሰጡን፣ ስናያችሁ ብቻ ቀለል ለሚለን
 
ግራ ቢገባችሁ እና ምታደርጉት ብታጡ በእጃችሁ ዳብሳችሁ አይዞህ ለምትሉ
 
ችሎታ ሳያንሳችሁ፣ በስራ ቦታ አለመመቻቸት እና የህክምና ቁሳቁስ እጥረት የተነሳ አቅመ ቢስ ለምትሆኑ፣
 
አቅመ ቢሱን ካርድ አውጥታችሁ ለምታክሙ፣ መድኃኒት መግዣ ለምትሰጡ (ከፋርማሲ ጓንት ስትገዙም አይቼ አውቃለሁ)
 
በሙስና እና ብልሹ አሰራር ባለሀብቶች ባቆሙት የግል ሆስፒታል ውስጥ ይህን አርጉ ይህን አታርጉ ትንሽ ብላችሁ ለምትሰቃዩ
 
እኛ ሰው ለመጠየቅ ወይ ለህክምና ገብተን እስክንወጣ በሚጨንቀን የሚሸት ሆስፒታል/ጤና ጣቢያ ውስጥ ውላችሁ ለምታድሩ
 
በውሃና መብራት መቆራረጥ ምክንያት ትንፋሻችሁ አብሮ ለሚቆራረጥ
 
ቾክ እንደ መድኃኒት እየታሸገ እና ጊዜው ያለፈበት መድኃኒት በኮንትሮባንድ ይገባ ዘንድ በየእርከኑ ያሉ ባለጊዜዎች ተባብረው፣ የምታዙት መድኃኒት ታማሚውን ሳያሽል ሲቀር ለምትዘለፉ
 
በተፈጥሮ በሆነ ችግር በተከሰተ ጉዳይ ነፍስ ለማትረፍ ስትረባረቡ ባለጊዜ፣ ሽጉጥ ለሚመዝባችሁ (ከአንድም ሶስት ታሪክ አውቃለሁ። አንዱ በዐይኔ ያየሁት ነው) እልህ በማጋባት ወይም በማስደንበር ሊፈጥር ስለሚችለው ችግር ሳይጨነቅ፣ እያሳየ ሚያስፈራራም አለ።
 
በሽታው በየቅያሱ በሰው እጅ ለሚፈጠርባችሁ። (ጀሶ እና ሳጋቱራ ከመብላት ይጀምራል)
 
በተለይ ከመዲናዋ ከአዲስ አበባ ውጭ ለምትሰሩ፣ ሰርታችሁ ለምታውቁ!
 
ክብር ለእናንተ!
 
በበረሀ ላይ እንዳለ ዛፍ፥ ጥላና ተስፋ ናችሁ።
 
ሕይወት እንደነበር፣ ሕይወት እንደሚቀጥል ማሳያ ምልክቶች ናችሁ።
 
በተለይ የአሜሪካ ሀኪሞችን እና የህክምናውን ሁኔታ ባየሁ ቁጥር ልቤ ስለአገሬ ነዋሪ እና ስለ እናንተ ትደማለች። በእናንተ ሁኔታ ውስጥ ቢሆኑ፣ ግማሾቻቸውም survive ማድረግ ይችላሉ ብዬ አላስብም። የድሀ አገር ሰው መሆን ደግነቱ ጠንካራ ቆዳ ይሰጣል።
 
በምንም ውስጥ ሁሉንም ሆናችሁ የመኖራችሁ ነገርም እየደነቀኝ፣ ለእናንተ ያለኝ አክብሮት እና ፍቅር ይጨምራል። ልታከም የሄድኩበትን ጉዳይ ድኜ፣ ድብርት እና የጥፋተኝነት ስሜትን እታመማለሁ።
 
የእውቀት ችግር አለባችሁ እንዳይባል፣ ከማንም እንደምትሻሉ በየሰው አገሩ የወጡ የሞያ አጋሮቻችሁ ምስክር ናቸው። እንኳን ሀኪም፣ በየትኛውም ዘርፍ ላይ ኢትዮጵያዊያን ከማንም አያንስም። አንገት አያስደፋም።
 
ይህንን ስል የግል የጠባይ ችግር ያለባቸውን ሁሉ አካትቼ አይደለም። ዳሩ ግን መልካም ስርዓት ቢኖር ኖሮ፣ በወል ከመጠራት ይልቅ እነሱንም ተጠያቂ ማድረግ ይቻል ነበር።
 
አቅም ካገኘሁ ከሀኪም ጓደኞቼ ጋር በነበረኝ ውሎ የታዘብኩ የሰማኋቸውን፣ በአንድ ዓመት የሆስፒታል ሥራ (በፐብሊክ ኸልዝ) ቆይታዬ ያየሁ፣ የሰማሁ የታዘብኳቸውን፣ የማስታውሰቸውን ጥቂት ታሪኮች ለመጻፍ እሞክራለሁ።
 
ዛሬ ግን ይኽችን መጫሬ፥ አይዟችሁ፣ በርቱ፣ ሀሳቤ ከእናንተ ጋር ነው ለማለት ነው!
 
ዛሬ ድንግዝግዝ ቢሆንም፣ ሲነጋ ብርሃን ይሆናል።
 
ትግላችሁ ለሰፊው ሕዝብ የተሻለ ህክምና ለማስገኘት እና፣ ለዘርፉ ተገቢው ትኩረት እንዲሰጠው በማስቻል ትውልድ የሚያጣጥመውን መልካም ፍሬ ያፈራልና ዛሬ በብዙ ብትደክሙ፣ ብትዘለፉ፣ የሚዲያ ዘመቻ ቢደረግባችሁም አይዟችሁ!
 
መንግስት ሰብስቧችሁ እናንተን አንኳሶ እና ‘ስለህክምና ቱሪዝም የማታስቡ’ ብሎ ተሳልቆ፣ ወላድ እናት ደም የነካው ጨርቋ እንዲታጠብላት መብራት እና ውሃ በሌሉበት ከተማ፣ አዲስ አበባን አስውባለሁ፣ “ወንዞቿን አጥባለሁ” የሚል የ”ቂጥ ገልቦ ክንብንብ” ስላቅ ቢያደርግም፣ አይዟችሁ።
 
እኛንም አትፍረዱብን! ስንመጣ የምናየው የእናንተን ፊት ነውና ስላለው ቁም ስቅል፣ ስለ ህክምና ቁሳቁስ እጥረት፣ ስለሙስናው፣ ስለሕይወታችሁ ባንድረዳ ይቅር በሉን።
 
ጂጂ እና ቴዲ አፍሮ ከጋሪሰን ሃውክ ጋር ከተጫወቱት ሙዚቃ ላይ፣ በእነዚህ የጂጂ መስመሮች ላብቃ!
 
“በቀን በቀን የሚያኖረኝ
ተስፋ ሳልቆርጥ የሚያውለኝ
ዕምነቴ ነው ያለኝ ብርታት
ተሥፋ አልቆርጥም
ተሥፋ አትቁረጥ
አይፈራም አይፈራም
ጎበዝ አይፈራም
ተሥፋ አይቆርጥም”
 
ቴዲም እንዳለው
 
“ሀሳብ አይሆንም አይባልም
ከሀሰብኩት እደርሳለሁ”
 
ካሰባችሁት ደርሳችሁ ለወገን የህክምናውን ዘርፍ ለወገን እና ለአገር እንዲጠቅም ታሻሽሉት ዘንድ ተስፋ አደርጋለሁ!

የምናፍቃቸው ዜናዎች…

06-Bidens macroptera - Adey abeba - 10-Verso Gimma-05-Mascàl-DSC01754
– መንግስት ከሕዝብ የሚሰበስበውን ግብር ገንዘብ አወጣጥ በተመለከተ ግልጽ የሆነ አሰራር መዘርጋቱን አስታወቀ። በዚህም መሰረት በመንግስት ጥሪ ተደርጎላቸው አገር ውስጥ ገብተው ለነበሩ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እና ግለሰቦች ይደረግ የነበረው የእለት እና የማረፊያ ወጪ እንዲቋረጥ እና፣ ግለሰቦቹ/ቡድኖቹ ራሳቸውን እንዲያስተዳድሩ ተወሰነ።
 
– ዘር እና ጎጥን መሰረት አድርገው ፓሪዎች እንዳይመሰረቱ፣ ጥብቅ አዋጅ ተላለፈ።
 
– ተቃዋሚ ፓርቲዎች መከባበር የተሞላበት ውይይት አደረጉ። ፓርቲዎቹ በየልሳኖቻቸው ያደረጓቸው ውይይቶች እና ክርክሮችም፣ ፍጹም መከባበር እና ለአገር በሚጠቅም መልኩ መተጋገዝ የታየባቸው ነበሩ።
 
– አድማጭ ተመልካቾቻቸውን ለማስፋት እና ስርጭቶቻቸውን በሰፊው ለማዳረስ በጋራ በነደፉት እቅድ መሰረት፣ ኦኤምኤን እና ኢሳት የ30 ደቂቃ የዜና ሽፋን ሰዓት በቅይይር ተሰጣጡ። በወቅቱ ሚዲያ ከሚዲያ ጋር ተደጋግፎ፣ ሀሳብን የመግለጽ መብትን ለማስረጽ መስራት እንደሚያስፈልግ ተገለጸ።
 
– አገሪቱ ላይ ባለው የመልካም አስተዳደር ጉድለት እና ፖለቲካዊ እና ወገናዊ ጥቅመኝነት የተቆጡ የአዲስ አበባ ወጣቶች መስቀል አደባባይ ፍጹም ሰላማዊ የሆነ የተቃውሞ ሰልፍ አድርገው፣ እስር እና ወከባ ሳይገጥማቸው በሰላም ወደየቤታቸው ተመለሱ። ፖሊስም ለሰልፉ በሰላም መጠናቀቅ ከፍተኛ ጥበቃ አድርጎ ሕዝባዊነቱን አስመስክሯል።
 
– አገሪቱ ውስጥ እየመጣ ባለው ለውጥ አማካኝነት 3 እስር ቤቶች ተዘግተው ረዳት የሌላቸው አረጋውያን መቆያ ተደረጉ።
 
– በስልጣን ዘመናቸው የሕዝብን ሀብት በመበዝበዝ እና ሰዎች ላይ ኢሰብአዊ ጥቃት በማስፈጸም የተሳተፉ ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለው በወንጀለኛ መቅጫ ህጉ መሰረት ቅጣት የተበየነባቸው ሲሆን፣ በወቅቱ ያፈሩት ሀብትም ተወርሶ ለሕዝብ ጥቅም ገቢ ሆኗል።
 
– ሰዎች ሀሳባቸውን ያለገደብ መግለጽ በነበራቸው ፍላጎት የተነሳ፣ በየማህበራዊ ድረ ገጹ ፌስቡክ ላይ የነበረው ትርምስ እና መሰዳደብ በመጥፋቱ፣ ወጣቶች ሀሳብን መሰረት ያደረገ ውይይት ላይ እንዲያተኩሩ እንዳገዛቸው ተናገሩ።
 
– ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ሁለቱ ብቸኛ ፓርቲዎች በቀጣዩ ምርጫ ላይ ከፍተኛ ፉክክር ያደርጋሉ። ከወዲሁ የምረጡኝ ቅስቀሳቸውን የጀመሩ ሲሆን፣ ምርጫ ቦርድም ለነጻ እና ገለልተኛ ምርጫ ዝግጅቱን ጨርሶ እየጠበቀ ነው።
 
– ጾታዊ ጥቃት እና ትንኮሳ የፈጸሙ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው ለተጠቂዎቹ ፍትህ በመሆኑ ደስታ የተሰማቸው ሰዎች ገለጹ።
 
– ኢትዮጵያ ውስጥ በተፈጠረው የስራ እድል እና ሞያን መሰረት ያደረገ ውድድር መሰረት ወደውጭ የሚሰደዱ ምሁራን ቁጥር ቀነሰ። ውጪ የሚገኙ ምሁራንም ወደ አገር ተመልሰው የተለያዩ የስራ መስኮች ላይ እየተሰማሩ ነው።
 
– ህብረት ለእድገት በተባለ የወጣቶች ማህበር ውስጥ ወጣቶች በተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች ላይ ተሰማርተው አስተሳሰብን የመቀየር ስራዎችን እየሰሩ ነው። በተለይም አገሪቱ ላይ ለረጅም ዓመታት ተንሰራፍቶ የቆየውን የት/ት እጥረት ለመቅረፍ፣ በክረምት እና በእረፍት ቀናቸው የማስተማር ስራዎችን ያከናውናሉ።
ወዳጄ ጋዜጠኛ ሀብታሙ ስዩም በጋበዘኝ መሰረት፥ የምናፍቀውን ዜና በስስ፣ ድፍርሱ እንዲህ አስፍሬያለሁ። እስኪ ደግሞ የምትናፍቃቸውን ዜናዎች እንድታጋራን ወዳጄ Emebet Lakewን ልጋብዝ።
Join the #mydreamnews campaign

መለስ፣ በረከት፣ አብዲ ኢሌ፣ ደመቀ መኮንን፣ ሼኽ አላሙዲን፣ ጭብጨባው፣ የዛሬ ደማሪ ተደማሪው፣ የትናንት አጋፋሪው ሁሉ፣ ኢህአዴግ ወዘተረፈ…

3-199x300
☞ መለስ የዛሬ 9 ዓመት፣ ኢህአዴግ ጉባኤውን ሐዋሳ ባካሄደ ወቅት “ኢህአዴግ እቅዱን ለማሳካት ቢያንስ እስከ 50 ዓመት በስልጣን ለመቆየት አቅዷል” ነገር ብሎን ነበር።
 
በ57 ዓመቱ ክልትው አለ!
 
☞ በረከት ስምዖን የዛሬ 7 ዓመት ገደማ፣ “የሁለት ምርጫዎች ወግ” የተሰኘ መጽሐፉን በሸራተን አዲስ ባስመረቀበት ወቅትም “ኢትዮጵያ እየተጓዘችበት ባለችበት የልማት ጐዳና ቀጥላ ውጤታማ ለመሆን 30 እና 40 ዓመታት ያስፈልጋታል” ብሎ ነበር።
 
ለጊዜው ከብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ታግዶ፣ የሰይፉ ፋንታሁን እንግዳ ሆኗል!
(ሰይፉ እና ሼኹ፤ ሼኹና በረከት
እንደ ጊዜው ፀባይ እንከረባበት…?)
 
☞ በመጽሐፍ ምረቃው ወቅት ከሼኹ ጋር ሲደናነቁ፣ ሲወዳደሱ ነበር። መለስም አልቀረ። ኢህአዴግ “የሕዝብ ፍቅር ያለው ፓርቲ” ተብሎም ነበር። እነ ዶ/ር ብርሃኑም በሰፊው ተብጠልጥለው እንደነበር በወቅቱ ሰምተናል። እሱ ያሰማራቸው ኮካዎችም ፌስቡክ ላይ ይጽፍ የነበረውን ወጣት መውጫ መግቢያ አሳጥተው ነበር።
 
የአላሙዲን ክፉ ደግ እንደተዳፈነ፣ ዶ/ር ብርሃኑ ወደ አገር ቤት ሊገባ ነው!
ኮካዎቹም፥ የሰሜኖቹ ገሚሱ አብን፣ ከሚሱ ድብን ብለው ሲከፈሉ፤ የወደምህራቦቹ የመሀል አገሮቹ ደግሞ በቲሸርት አሸብርቀው “ተደምረናል” ብለውናል!
 
☞ “ደራሲዎች፣ ድምፃውያን፣ ቲያትረኞች፣ የፊልም አክተሮች፣ ሰዓሊያን፣ የማስታወቂያ ባለሞያዎች፣ ጋዜጠኞች፣ ባለሃብቶች፣ የኢህአዴግ ባለሥልጣናት እና ሌሎች ተጋባዦች አዳራሹን ሞልተውታል። …መቀመጫዎቹ በሙሉ ተነስተው እድምተኛው ቆሞ የዝግጅቱን መጀመር ይጠባበቃል።” ብላን ነበር ፕሮግራሙን የታደመችውና ሁኔታውን በአዲስ አድማስ ጋዜጣ አካፍላን የነበረችው Tsion Girma Tadesse (ጺዬ፥ ከትናንት በስቲያ ስጽፈው ጽሁፉ ያንቺ እንደነበር ስለተዘነጋኝ ይቅር በዪኝ)
 
ዛሬስ አማን ነው? ወደ ቤመ “ቦታ ቀየረ እንጂ ድሮም ሞቶ ነበር” ዓይነት ሳይሆን አይቀርም።
 
☞ በዕለቱ የክብር እንግዳው በወቅቱ የት/ት ሚኒስቴር የነበረው፣ አሁን ደግሞ “የለውጡ አጋፋሪ” አቶ ደመቀ መኮንን ነበር። “ተመራማሪዎችና የተለያዩ ተቋማት በኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊና የልማት ተቋማት ላይ ለመመራመር እና የዳበረ ሐሳብ ለማምጣት የአቶ በረከት መጽሐፍ መነሻ ሊሆናቸው እንደሚችል እምነታቸው እንደሆነ ገለፁ።” ተብሎም ነበር።
 
የት/ት ፍኖተ ካርታው ላይ በማጣቀሻነት ተካቷል ወይ?
 
☞ “የመጽሐፉ፤ መታሰቢያነት ለትግሉ ባለቤቶች፣ ታጋዮች፣ የልጅነት ዕድሜያቸውን ለሠላምና ለዴሞክራሲ በተለይ በትግሉ ወቅት ላሳለፉት ታላቅ ከበሬታ የሰጠ እና ለማስታወስ ያለመ ነው” ብሎም አክሏል አቶ ደመቀ! ታዛቢዋ “አቶ ደመቀ የገለጿቸው ታጋዮች በአቶ በረከት መጽሐፍ የቱ ጋር እንደተጠቀሱ ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም።” ብላን ነበር።
“በምን አወቅሽበት በመመላለሱ
ሲታሰር ወደ እኔ፣ ሲፈታ ወደሱ”
 
አላሙዲንም ታስሯል፤ በረከትም ከስሯል፤ አንድ ለእናቷ አላሙዲን ላይ “የተነበየችው” እህተ ማርያምም ንግስተ ነገስት ነኝ ብላለች! ሃሃሃ…
 
☞ “ኢህአዴግ አስተዋይ እና አገሪቷን ከእንቅልፏ የቀሰቀሰ ድርጅት ነው” በማለትም ፓርቲያቸውን አሞካሹ። በሕዝብ ስለመፈቀሩ እና ስለመመረጡም መወራቱን ነግሮን ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይም ስለኢህአዴግ የተመሰከረ ዊዝደም ነግረውናል።
ኢህአዴግ ወይም ሞት!?
☞ አላሙዲንም በዕለቱ፥ “አንዳንድ ሰዎች ኢህአዴግን ትወዳለህ ይሉኛል። አዎ! እወዳቸዋለሁ አራት ነጥብ።…”
 
“አቶ በረከት እንዳለው ደቡብ አፍሪካ ሄጄ ጠይቄዋለሁ፤ የጠየኩት ግን አመፀኛ እና ልውጣ ብሎ ስለሚያስቸግር ነው። ታከም፣ እረፍ ሲባል እሺ አይልም። እኔ ደቡብ አፍሪካ ሄጄ መጀመሪያ ያደረኩት ክፍሉን በሴኪዩሪቲ ማስከበብ ነበር። እሱ ግን በኋላ የብአዴን 25ኛ ዓመት በዓል ላይ ካልተገኘሁ ብሎ አስቸገረ ቃል አስገብቼ ይዤው መጣሁ። በ48 ሰዓት ውስጥ አንጠልጥዬ መለስኩት፤ እኔን የሚያሳስበኝ የጤናቸው ጉዳይ ነው።” በማለት ሚስጥራቸውን አጫወቱን።
የድርጅት ፍቅር!?
“እንደዚያ ስወድሽ፣ አብልጬ ከራሴ
ያሰብሽው ሲሞላ፣ ከዳሽኝ ወይ ነፍሴ?
ይህቺ ናት ወይ መልሴ ዳራራራን ዳራን”
 
አብዮት ልጆቿን ትበላለች! ምጽ ምጽ
☞ “በመጨረሻም ሼኽ መሐመድ “እስከ ህይወት ፍፃሜ ድረስ አብረን ነን” ሲሉ ማሉ። አቶ በረከትም በጭብጨባ መሐላውን አፀኑላቸው። ታዳሚውም አጨበጨበ። አጨብጭቦም ወደ ቤቱ አልሄደም። “ምን ጠፍቶ” የተባለለትን የሸራተንን ድግስ እስኪበቃው ተቋደሰ።” ብላን ነበር ጺዮን።
“ሩቅ አሳቢ፣
ቅርብ አዳሪ”
 
☞ የዛሬ 7 ዓመት በ40 ዓመት እንቆያለን ወሬው በሽተንጨርጭሬቄ ይኽችን ጭሬ ነበር፤
 
እዚህ ቅርብ ነውና፣ የሩቅ አሳቢ አዳሩ፣
በምኞቱ ልክ ይሰንዝር፣ ላይቀር ሳይደርስ ማፈሩ፣
ለማይቀር ቀኑ ሲመጣ፣ በሰፈሩት መሰፈሩ፣
በገባቸው ልክ ያርዱ፣ በክሳቸው ያሸብሩ፣
ቀለም አይዝለቃቸው፣ በድንቁርና ይኑሩ።
 
ከጥፋት ውሃው ለመዳን፣ ኖህ መርከቡን ሲሰራ፣
አርባ ዓመት አለን ብሎ፥ ነበረ ህዝቡ ሚያሽላላ፤
 
ወትሮም የሰነፍ ሰው እቅድ፣ ስንፍናውን ነው ሚያጎላ፣
አለመስራቱን ነው ሚያሳይ፣ ነውሩን ገላልጦ ካውላላ፤
እንደተቀጡ ያኔ፣ የሃሰት ወሬ ሲነዙ፣ ከነዓንን ሰልለው፣
የገለሞተ በድን ላይ፣ ዛሬም እግዚአብሄር ፈራጅ ነው።
 
ስለ 1 ቀን 1 ዓመት፣ ስለ 40ው 40ዓመት መዝዞ፣
በድናቸውን ይጣለው፣ በምድረ በዳ አቅበዝብዞ።
 
☞ አሜን!! ለጊዜው የ”ተደማሪው” አብዲ ኢሌን መያዝ ሰምተናል። ፍርዱንም ፍትሃዊ ያድርግልን። ያቀላጥፍልን! ሌሎቹም እንዲሁ ወግ ወጉን ይዩ!
 
☞ በረከት ስምዖንም የዛሬ 4 ዓመት “የወደፊቱ የህዳሴ መንገድ” በሚል ርዕስ ለኢህአዴግ ካድሬዎች ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሁፍ። “ኢህአዴግ ልማቱን ለመጨረስ ከ40 እስከ 45 አመት ያስፈልገዋል” ብሎ ነበር።
 
እንግዲህ 40/60ም ቤት የለኝም እያለ ነው፤ አርብ አምሳ እያለ ሲያዝገን የኖረው።
☞ ይልቅ፥ በመጽሐፍ ምረቃው ወቅት አላሙዲን “መጽሐፉን አላነበብኩትም ግን ለመጭው ትውልድ እንደሚጠቀም አምናለሁ” ሲሉ፥ “ሳያዩ የሚያምኑ ብፁሃን ናቸው” ብለን ተሳልቀን ነበር።
 
መቼም እስር ቤት ውስጥ ሰው ያነባልና ይኽኔ ጨርሰውት ይሆናል። በረከትም በርሳቸው አስተያየት ተበረታትቶ ይሆናል 2ኛውን መጽሐፍ ጀባ ያለን።
 
☞ ከጠፍጥፎ አዳሪነት
ወደ ጥፎ አዳሪነት ለመሸጋገርም የሚያበቃ ደግነት የለውምና፣ ፍትህ እንዲፈጸም እንናፍቃለን!
 
እስከዚያው ግን፣ እርስበርስ ለመማር እና በርትዕው ለመጓዝ ከበቂ በላይ ትምህርት እየቀሰምን ነው ያለነውና ትንሽ ጆሮ እና ልቡና ይስጠን።
ያው ኢህአዴግ እነተባለለት 50 ዓመት ፖዚሽን እየቀያየረ ያጫውተን ይሆንን? እስኪ አብረን እንከታተል!
 
ትምህርቱስ ሙሉ ነበር
የሚማረው ሰው ቢኖር!

ልደ ቱ!

23519141_2009666822383122_4032006682889241508_nጋሽ ስብሀትን አንድ ጋዜጠኛ
“ከቅርብ ጊዜ ዘፋኞች የምትወደው” ሲለው
“ይኼ ነይልኝ…የሚለው ልጅ ይመቸኛል“
ጋዜጠኛው ቀጠል አድርጎ
“የማይመችህስ ዘፋኝ?” ሲለው
“ከእሱ እየተቀበለ “ነይለት” የሚለው አቃጣሪ” አለው አሉ።

ይኼን ያስታወስኩት ዮሴፍ ገብሬ (ጆሲ) እና ያ ቀልማዳ ልደቱ አያሌው ያወሩትን ዞር ዞር ብዬ ተመልክቼው፥ አንዴ ጆሲን፣ አንዴ ልደቱን እያልኩ መመዘኑ ሰለቸኝና ነው።

ቃለ መጠይቁ ሲጀምር እና “የፍቅር እስከ መቃብር ደራሲ ማነው?” በሚል ጥያቄ ነው። ተመልካቾች በ2 ብር (?) የጽሁፍ መልእክት ሰዎች ምላሽ እንዲሰጡና፣ ከመካከላቸው አንዱ ስጦታ እንደሚበረከትለት ይገልጻል። ማስታወቂያው በየመሀሉም ለብዙ ጊዜ ይደጋገማል። የመጀመሪያው መላሽ ለሚሸለም ያን ያህል መደጋገሙስ ለምን አስፈለገ? ማለቴ አልቀረም። በሁለተኛው ክፍል ደግሞ ጥያቄው “ይኽች አርቲስት ማን ትባላለች” ብሎ የእንግዳዘርን ምስል ነው የሚያሳየው።

ብቻ ሕዝቤ በነፍስ ወከፍ ሁለት ሁለት ብሯን አዋጥታ ታበረክታለች። ይመቻቸው!

የመጽሐፍ ነገር ሲነሳ፥ የሁለተኛ ዓመት ተማሪ ሳለው መምህሬ የነበረና፣ አሁን የቅርብ ወዳጄና አማካሪዬ ጋር ከሳምንታት በፊት ስናወራ በጨዋታ መሀል ያነሳብኝ ነገር ትዝ አለኝ።

ከወዳጄ ጋር የነበረን ጨዋታ፥ እንደአገር ስላለመታደላችን፣ ይኽ ነገር የሚቆምበት ጊዜ እንደሚናፍቀን፣ እንዲሁም ድርሻችንን ለመወጣት በየዙሪያችን ራስን ከመለወጥ አንስቶ መሞከር እንጂ፥ የሚታይ የሚሰማው ነገር ሁሉ ተስፋ አስቆራጭ ስለመሆኑ ነበር። ነገርን ነገር አንስቶት ወዳጄ ጆሲን አስታወሰው።

“በጣም ነው የሚያሳዝነው። የሚዲያ ባለቤት እንኳን ለእፍረት ብሎ ስለንባብ የሚገነባ ነገር አያወራም።

አሁን ባለፈው ጆሲ የሚሉት ልጅ ከአንድ ሌላ ጋዜጠኛ ጋር ያወራል። ጋዜጠኛው “መጽሐፍ ታነባለህ ወይ?” ብሎ ይጠይቀዋል።

“አሁን አላነብም። ድሮ ግን አነብ ነበር።” አለው ኮራ ብሎ።

“እስኪ ድሮ ካነበብካቸው መጽሐፍት ያንዱን ርዕስ ንገረን” ሲለው፥

“አሁን ትዝ አይለኝም።” አለው።

ምናለ የአንዱን መጽሐፍ ርዕስ እንኳን ቢጠራ? ቢቀር ፍቅር እስከ መቃብር አይልም ሰው? እንግዲህ ይኽ የሚዲያ ባለቤት፣ ጋዜጠኛ እና ዘፋኝ ነኝ የሚል ሰው ነው። ሌላውን ደግሞ አስበው።” ተባባለን፣ መዓዛ ብሩን አወድሰን አለፍን። (ባይጠቅመኝም ሌላ ቃለ መጠይቁን የሰማ፥ ወይ ከማን ጋ እንደሆነ የሚያስታውስ ካለ ቢነግረኝ እና ብሰማው ደስ ይለኛል።)

መዓዛ ብሩን ስናወሳ ስለእንግዶቿ ያላትን ጥልቅ እውቀት እና፣ ስለሰሩት ነገር ለማወቅ ጥናት/ምርምር ስለማድረጓም ጭምር ነው።

ይኽን ማንሳቴ ደግሞ ጆሲ ስለእንግዳው እንዴት ጥናት አያደርግም? ቢያንስ ከጻፋቸው መጽሐፍት አንዱን በወፍ በረር ቃኝቶ ማውራት ቢቀር፥ እንዴት ስለመጽሐፎቹ እሱ እንዲናገር እንኳን የመጽሐፉን ወሬ አያነሳበትም?

ጭራሽ ስለመጽሐፍና ንባብ፣ ስለጻፈው ልብወለድ ሲያነሳበት ሁሉ፥ የጆሲ ልብ ፔጆዋ ላይ ነው ጆፌ ብላ የቀረችው።

ብቻ ያው ነው።

ጆሲ “ሰማሁ… አሉ…”

ልደቱ “አልኩ… አደረግኩ… እኔ መሲሁ ነኝ። ልወደድ አልልም። ሕዝቡ ይወደዋል አይወደውም አልልም። እኔ ካመንኩበት እናገረዋለሁ።”

ያው መበጣረቅ ነው!

ሕዝብ ካልወደደው ለአገር ምኑን ጠቀመ? “አገር ማለት ሰው ነው” እንደሚባል አያውቅም ማለት ነው? ለነገሩ፥ ቤቴ ውስጥ ይሉኝታ ያጠቃኛል። በፖለቲካ ግን ይሉኝታ አላውቅም ብሎ ነገሩን ሲጀምር ነበር ማቆም የነበረብኝ።

የተቸገርነው እኮ አገሪቱን እንደቤታቸው አላከብር እያሉን ነው። ሕዝቡን እንደወገናቸው አልቆጥር እያሉን ነው።

ይኽን ስጽፍ ፌስቡክ “የዛሬ ዓመት ምን ብለህ ነበር” ቢለኝ ጥሩ ነው?

እንደው… የሞት የሽረት “ግድ መምረጥ አለብህ” ብባል፥ አይደለም ከሌላ ሌላው…

“መለስ ዜናዊ ከልደቱ አያሌው ብዙ ጊዜ ይሻለኛል!” እላለሁ! Period! ብለህ ነበር ይለኛል።

ምድረ አተቲያም፥ “የአረም እርሻ” ገበሬ! ጆሲን ግን ጥሩ ለጎም ለጎም፣ ጎተት ጎተት አድርጓታል። ሃሃሃ…

እኔማ ከ1992 ዓ/ም (ለመጀመሪያ ጊዜ ቲቪ ላይ ካየሁት ጊዜ) “ሆኜ፣ ተደርጌ” ሲል ሰምቼው እንደቀፈፈኝና ቀልማዳነቱ ብቻ እንደሚታየኝ አለ። He is one of the persons/things that time and time prove my instinct right.

ሃሌሉያ!