ኢህአዴግ ጋዝ የነካው ምግብ…

ኢህአዴግ ጋዝ የነካው ምግብ ነው ስንል በምክንያት ነው። የጥቅም እና ዝርፊያ ተካፋይነቱን ሕወሃት የበላይ ሆኖ ቢሰፍርበትም፥ ትናንት ሁሉም በተመቸው እና ጊዜው በፈቀደለት ልክ ዘግኗል፣ አንገላቷል፣ በየፈርጁ እና በየደረጃውም፥ የግፉም የዝርፊያውም ተካፋይ ነበር። የሚደርሰው ወንጀል እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሁሉ እንዳይታወቅ በመሸፋፈን ረገድም ሁሉም አባል ይኽ ነው የማይባል ሚና ተጫውቷል። ምንም እንኳን በሕወሃት የበላይነት ቢዘወርም፥ የሰብአዊ መብት ጥሰቱን እና ንጹሐንን የማፈኑን ሥራም በድርጅት ደረጃ አቋም እና አተገባበር ይዘው ሲያደርጉት የነበረው ነውና፣ የጭንቀት ቀን ሲመጣ ጣት መቀሳሰሩ በኅሊና ዳኝነት ፊት የትም አያደርስም። ማናቸውም አሸባሪውን ድርጅት ሲያገለግሉ እንጂ፣ ገዳም አልነበሩም።

ሁሉም ደርሶ በድል አጥቢያ አርበኝነት ስሜት እና በለውጠኝነት ሽፋን ጣት ቀሳሪ ይሁን እንጂ፣ ለመዛኝ እና ለፈራጅነት የሚያበቃ ንጽህና ያለው ያን ያህል አይደለም። ምንም አያውቅም የሚባለው አባል እንኳን፣ ቢያንስ ዝም በማለት እና ንጹሐን ሲንገላቱ ባለመከላከል፣ ድሀ ሕዝብ ሲመዘበር የምዝበራው አበል ተካፋይ በመሆን እያመሰገነ እና፤ አባል ያልሆኑና ያገባኛል ያሉ ሰዎችን በጠላትነት እየፈረጀ ኖሯል። የኢትዮጵያ አምላክ ራቁት እሲያስቀር፣ የጊዜ ፈረስ እንዲህ በአፍጢም እስኪፈጠፍጥ ድረስ!

በርግጥ፥ አንድም ይሁን ሁለት፣ ያጠፋ ሰው መጠየቅ መጀመሩ አግባብ ነው። ሆኖም ግን፥ የሌላው ነውረኝነት አለመጋለጥ፣ የተጋለጡትን እና በህግ ለመጠየቅ መንገድ የተጀመረላቸውን ሰዎች ጉዳይ ስህተት አያደርገውም። ዛሬ ጊዜው ፈቅዷል፣ ትናንት አልፏል በሚል ቀመር፥ አብረው ሲፈተፍቱ፣ የሕዝብ ደም ሲገብሩ እና ነውሩን ሲጋርዱለት፣ በታማኝነት እና ቁርጠኝነት ሲያገለግሉት የነበሩትን ድርጅት “እኔ ከደሙ ንጹህ ነኝ” በሚል ጲላጦሳዊ ግብዝነት ሲነዛ ግን፥ አሁንም ህሊና ካለ ይፈርዳል።

እንደማሳያ፥ ሰሞኑን በድፍረታቸው እና አጋላጭነታቸው ተደንቀን፣ አፋችንን ከፍተን ሀቀኝነታቸውን የመሰከርንላቸውን አምባሳደር ሱለይማን ደደፎን የትዊተር ገጽ በጊዜ ወደ ኋላ ተመልሰን በመቃኘት ነገሬን ልቀጥል።

አቶ ሱለይማን ዛሬ ፓርቲአቸው ኦህዴድ የበላይ ባይሆን እና ሕወሃት ቢቀጥል ኖሮ፣ ሰጥ ለጥ ብለው የሚገዙ እንጂ “ግፍ አንገፈገፈኝ” ብለው የሚለቁ አይነት ነበሩ የሚያስችል የጀርባ ታሪክ እንዳላቸው የሚያሳይ ማስረጃ የለም። በርግጥ እሳቸው ብቻ ሳይሆኑ፣ ሌሎች አባላቶችም እንዲሁ ከመጣው ጋር ቀጥለው፣ በጥሎ ማለፍ ድርጅታቸውን እያሽሞነሞኑ ይቀጥሉ እንደነበር መገመትም ከባድ አይደለም። ድርጅታቸው ኢህአዴግን በታማኝነት ከማገልገል ባለፈ፥ ሲያደርግ የኖረውን ነገር በመሸፋፈን እና ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በማሳጣት የተጫወቱት ሚና ብዙ ነው።

በኦክቶበር 2013 የአፍሪካ አገራት በኢትዮጵያ መንግስት አዘጋጅነት፣ እነ ኡሁሩ ኬኒያታ የሰው ልጆች ላይ ወንጀል በመፈጸማቸው  በሚል መከሰሳቸውን ለመከላከል፥ በአዲስ አበባ አስቸኳይ ስብሰባ አድርገው ነበር። አጀንዳቸውም የዓለማቀፉን የወንጀል ፍርድቤት International Criminal Court (ICC) ለመቃወም ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በተባበሩት መንግስታት ስብሰባ ተገኝተውም ፍርድቤቱን መተቸታቸውን ተከትሎ፥ የአፍሪካ መሪዎችን ስብሰባ ጠርተው ነበር። ነገሩ “ነግ በእኔ”፤ “አፍንጫ ሲመታ አይን ያለቅሳል” ነበር። በተለይ ደግሞ የነገሩ ጠንሳሽ ኢትዮጵያ መሆኗ “ፈስ ያለበት ዝላይ አይችልም” ዓይነት ነበር።

ታዲያ ያንን ተከትሎ፥ ከሁለት ወይም ከሶስት ሳምንታት በኋላ በኦክቶበር 28 ቀን፥ አቶ ሱለይማን

I am skeptical on the very intention to create the ICC. Why doesn’t it open its eyes on the whole globe than giving excess attention to Africa?

በማለት ለአምባገነኖቹ የአፍሪካ መሪዎች መቆርቆራቸውን ገልጸው ነበር።

1

ኖቬምበር 15 ቀን 2013፥ የሳውዲ አረቢያ መንግስት በኢትዮጵያውያን ላይ እየደረሰ የነበረውን ስቃይ እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት በማውገዝ፣ ሰማያዊ ፓርቲ በሳውዲ አረቢያ ኤምባሲ ደጃፍ ላይ ለማካሄድ በጠራው የሰላማዊ ሰልፍ ላይ የወጡ ሰዎች፣ ላይ ፖሊስ የተቃውሞ ሰልፉን በመከልከል ሰዎችን ደብድቦ እና አስሮ ነበር።  ታዲያ በዚያን ቀን፥ አቶ ሱለይማን

Ethiopian Gov’t has allocated 50 million Birr to integrate Ethiopians deported from Saudi Arabia. But what do the opposition parties are doing? Ethiopian opposition parties are trying to benefit out of tears of Ethiopian migrants in Saudi Arabia as usual. Why?

ብለው በሁለት ትዊት ጽፈው ነበር።

2.jpg

በመጀመሪያ የኢትዮጵያ መንግስት ገንዘቡን የመደበው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ንብረት ላይ መሆኑን ዘንግተውት እንደልግስና ቆጥረውት ተመጻድቀው ነበር። ገንዘቡ በአግባቡ ይዋል አይዋልም አይታወቅም። ሆኖም ግን፥ በወቅቱ ለወገን በመቆርቆር የተጠራን ሰልፍ ተከትሎ፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን በጅምላ ለመፈረጅ እና፣ እንደ ኢህአዴግ አባልነታቸው “ተቃዋሚዎች በሕዝብ እንባ ለማትረፍ የሚሞክሩ ናቸው” ብሎ ስም ለመለጠፍ እና፣ “መንግስት ይህን ሲያደርግ፣ እነሱ ግን ምንም እንዳላደረጉ” ለማጉላት ዳክረው እንደነበር እናያለን።

20131115163925420734_20

(እንደፓርቲ ከአባላት ከሚያገኙት መዋጮ ላይ መቋቋሚያ እንዲሰጡ ጠብቀው ነበር ማለት ነው። እንደተቃዋሚ ፓርቲነታቸውም ለዜጎች ጥቃት መቆርቆራቸውንም አቃለዋል።) ከዚህ በላይ ኢህአዴን መጋረድ እና የሰብአዊ መብት ጥሰቱን መደገፍ ከየት ይመጣል?

እነ ወ/ሮ ሚሚ ስብሀቱ፣ አቤል ተስፋዬ እና መርከብ ነጋሽ ተሳትፈውበት በነበረ “የቀለም አብዮት” ዶክመንተሪ ማግስት፥ የዞን 9 ስድስት ጦማርያን እና 3 ጋዜጠኞች ወዳጆቻችን በአፕሪል 2014 መታሰራቸውን ተከትሎ፥ አቶ ሱለይማን፣ በሜይ 1 2014፥

Zone Niners are messangers of color revolution hired by neo-liberal masters. They are instructed to create violence ahead of next election. Press Freedom is not systematic invasion or campaign to change regime by color revolution. That is what the west are trying in Ethiopia.

ብለው ንጹሀን ላይ ጣታቸውን ቀስረው፣ እና የመንግስትን ጭቆና ለመሸፈን ሞክረው እንደነበርም እናስታውሳለን።

4.jpg

የመንግስትን የተጋነኑ “የኢንቨስትመንት” ወጪዎችን በተመለከተም፥ በዲሴምበር 3፣ 2014

Where will huge state investments lead Ethiopia? Obviously to growth

ብለው ጽፈው ነበር።

6

እንግዲህ ወደ እድገት ያመራናል ያሏቸውን ወጪዎች በተመለከተ ነው፣ አሁን ያላየ፣ ያልሰማ ሆነው በጻድቅ ምስክርነት የቆሙት። ምስክርነት መቆማቸውን መንቀፌ አይደለም፣ ነገር ግን ትህትና የቀላቀለ ቢሆንና፣ ሁላቸውም መነካካታቸውን የማይክድ መንፈስ ያረበበት አነጋገር ቢሆን የሚል የከሸፈ ጉጉት እንጂ።

በሌላ ማሳያ፥ የአሁኑ የጠቅላይ አቃቤ ህግ፣ የያኔው የፍትህ ሚንስትሩ አቶ ብርሃኑ ፀጋዬ፥ በ2011

ያለ ፍርድቤት ትዕዛዝ አይታሰርም። ያለፍርድቤት ውሳኔ አይቀጣም። በምርመራ ወቅት ድብደባ የለም። ግርፋት የለም። ሕገመንግስታችን ይከለክላል። እነዚህን ነገሮች ማለት ነው። ስለዚህ እንደዚህ ተደርጓል፣ እንደዚህ ተደርጓል ተብሎ አሉባልታ ካልሆነ በስተቀር በተጨባጭ እንደዚህ አይደረግም። በማረሚያ ቤት የሚገኙ፣ በምርመራ ላይ የሚገኙ፣ በፍርድቤትም የሚገኙ ማየትም፣ መጎብኘትም ይቻላል። እየተደረገም ነው። በውስጥም በውጭም ባሉት አካላት ነው። በዋናነት ለነዚህ አካላት አይደለም መንግስት እነዚህን ስራ የሚሰራው።

በዋናነት፥ ቅድም እንዳልኩት፣ ህገመንግስቱ ላይ የተቀመጡትን መብቶች የማስከበር፣ የማክበር ኃላፊነት የመንግስት ነው። ይሄም ህግ የወጣው፣ [የዜጎችን] መንግስት ሌት ተቀን እየሰራ ያለው፣ የዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስከበር ነው እንጂ ሌሎች ሶስተኛ ወገን የውጭ አካላትን ለማስደሰት፣ ወይ ደሞ ለማስቀየም አይደለም። ለዜጎች፣ የዜጎችን መብት ለማስጠበቅ፣ በአገራችን ውስጥ የዴሞክራሲ ስርዓት ስር እንዲሰድ ለማድረግ ነው እየተሰራ ያለው እንጂ፤ ለነዛ አካላት ተብሎ የሚሰራ ነገር አይደለምና፣ ጣልቃ የሚገባበት ነገርም አይኖርም።

ባሉበት አንደበታቸው፣ ባለፈው ሳምንት በቁጥጥር ሥር የዋሉ ሰዎችን አስመልክቶ የሰጡት መግለጫ ላይ፥ ይደርስ የነበረውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት የገለጹበትን መንገድ እናስታውሳለን። ቪዲዮውን እዚህ ይመልከቱ።

የበፊት ንግግራቸው መታወሱ ሲወራ፣ ወዲያውኑ ዋልታ የያኔውን ቪዲዮ ከድረ ገጹ ላይ ወዲያው ያነሳው ቢሆንም፣ ቀድመው ያወረዱት ሰዎች እየተቀባበሉት ተመልክተነዋል። (ዋልታስ ቪዲዮውን ማንሳቱ ምን ይባላል?)

እንግዲህ በደም የተጨማለቀ ስርዓትን በሀቀኝነት ማገልገል እና ሲደርስ የነበረውን ግፍ እና በደል ሁሉ፣ የሰብአዊ፣ የዴሞክራሲ እና የሕገመንግስት ሽፋን በመስጠት እንዳልነበሩ፥ አሁን ሌላው ላይ በሚናገሩት ነገር ህሊና ቢኖር ኖሮ አይሸመቅቅም ነበር ወይ?

ከላይም እንዳልኩት፥ ትናንት እንዲህ ተደርጎ ነበርና ዛሬ ዝም ይባል አይደለም። ቢያንስ ግን፥ ትናንት ተሳትፎ የነበራቸው፥ ከጋዜጠኛ እስከ ባለስልጣን፤ ከተራ አባል እስከ ፈላጭ ቆራጭ ድረስ፥ “ስላልተጋለጥን/ስለማንጋለጥ” በሚል ስሜት፥ ወይም በኖሩበት የአድርባይነት ስሜት፣ ነገሮችን ሲተርኩ፣ ፍጹም ከደሙ ንጹህ መስለው ለመታየት የሚያደርጉትን ነገር በልኩ ቢያደርጉት የሚል ነው። አሁንም ተጠያቂነት ድንበር አይኑረው!

እንግዲህ መመዘዝ የተጀመረው የሙስና እና የሰብዓዊ ጥቃት ክር የት ጋ እንደሚቆም በጉጉት እና በሌሎች በራሪ እንስሳዎች እናያለን! 😉

ዕድሜና ጤና ይስጠን እንጂ ከጊዜ ዳኝነት ማንም አያመልጥም!

ሰላም!

ስለ24 ዓመቷ ሌንሴ ኔሜ ሹመት

 

43371204_2460431533973313_7357390166161358848_n

የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስኪያጅ (CEO) ተደርጋ የተሾመችውን፣ የ24 ዓመቷን ሌሊሴ ኔሜ በተመለከተ መረጃውን ማጋራታችንን እና ነገሩን ማውገዛችንን ተከትሎ፣ በግራም በቀኝ ወዳጆች አስተያየት ሰጥተዋል።

 
ነገሩ ያስቆጣቸው በርካቶች የመኖራቸውን ያህል፣ በገራገርነት ተመልክተው “ከቻለች ምን ችግር አለው? ወጣት ወደ ሀላፊነት ሲመጣ ማበረታት ነው ያለብን” ዓይነት ሀሳብ የሰጡም አሉ።
 
ከዚያም አልፈው፣ ጽሁፉ ኦሮሞ ስለመሆኗ በማይገልጽበት ሁኔታ፥ “ገና ለገና ኦሮሞ ስለሆነች፤ የኦሮሞ ስም ስላላት” ብለው በልባቸው የሚያስቡትን (ምናልባትም እየሆነ ያለውን ስለሚታዘቡ) የተናገሩም አሉ።
 
ባረጀ ባፈጀ ማሸማቀቂያ “ኦሮሞፎቢያ” ያሉም አሉ። እንደዚህ እያልን እውነትን የምናፍንበት እና የምናሳቅቅበት ጊዜ ሳያልፍ አልቀረም። ስለኦሮሞነቷ ነው ብሎ ከማሰብ ይልቅ፣ “ከእሷ የተሻለ ለቦታው የሚበቃ ኦሮሞ ስለሌለ ነው ወይ?” ብሎ መጠየቅስ አይቀልም ነበረ? 
 
አሁን ማንሳት የፈለግኩት ግን ነገሩን በበጎ ተመልክተው “ምን ችግር አለው? ዋናው ብቃት ነው እንጂ ዕድሜ አይደለም። እስከቻለች ድረስ ትሁና።” ያሉትን ነው።
 
በመጀመሪያ እንደዚህ ያለ አገር አቀፍ ዋና ፕሮጀክት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሀላፊ (CEO)
መሆን ከልምድም ከእውቀትም አንጻር የሚጠይቀው ብዙ ነገር አለ። የነገሩን ትርጓሜ፣ የሚሰጠውን ሀላፊነት እና ዓለም ላይ እንዴት ነው የሚስራበት የሚለውን መፈተሽ ተገቢ ነው።
 
ብስለት እና አመራር ጋር ሲመጣ፣ ዕድሜ ቁጥር ብቻ አይደለም። የሚያሸክመው ልምድ፣ እውቀትና ብስለትም አለው። 24 ዓመት ተለዋዋጭ ፍላጎት እንኳን ጠርቶ ቦታ ይዣለሁ የማይልበት፣ ከራስ ጋር ተስማምተው የማይጨርሱበት ዕድሜ ነው።
 
እንደዚያ ባይሆን እንኳን፣ ከተመረቀች 2 ዓመት የሆናትን ወጣት ለዚህ ቦታ ለመሾም፣ መስፈርቱ እሷ የምታሟላውን ያህል ብቻ ሲሆን ነው። ካልሆነ ግን ቢያንስ ያስተማሯትም አሉና፣ የት ባሳየችው የአመራር ብቃት ነው ተመራጭ ሆና ለሹመት የምትበቃው?
 
(በርግጥ የሌንሴ የሹመት ሙስና እና ፖለቲካዊ አድልዎ የጀመረው ከዩኒቨርስቲ ከመመረቋ በተሰጣት ሹመት ነው። እንደዚያም ሆኖ እንኳን፣ ዩኒቨርስቲ ውስጥ የማስተማር ስራዋን ሳትተው፣ ዋና ስራ አስኪያጅነቱን ደርባ መስራት መቻሏም ሌላ አነጋጋሪ ጉዳይ ነው። ካልተሳሳትኩ፣ የስራ አጡ ቁጥር ባሻቀበበት አገራችን ላይ፣ ሁለት የመንግስት መስሪያ ቤት ተቀጥሮ መስራት በህግ የተከለከለ ነው። በዚያም ላይ በእንደዚህ ያለ ከፈተኛ የአመራር ስራ ላይ ያለ ሰው፣ መኪና የመንዳትን ስራ እንኳን ደርቦ እንዳይሰራ ጥንቃቄ ይደረግለታል።)
 
ቦታው የተሰጣት በሹመት ነው እንጂ፣ ማስታወቂያ ወጥቶ ሰዎች አመልክተው፣ በነጻ ተወዳድረው እና በገለልተኝነት ተመዝነው አለመሆኑ ነገሩን ከብቃት እና ከእውቀት ጋር እንዳናያይዘው ያደርገናል። ምናልባት እርሷ የትምህርት ቤት ጓደኞች መካከል (የዛሬ 2 ዓመት የተመረቁ) የመጀመሪያ ስራ እንኳን ይዘው የማያውቁ ይኖሩ ይሆናል። በጣም ችሎታ እያላቸው፣ በፓርቲ ተሳትፎ እና ትውውቅ የተነሳ ስራ አጥተው ባክነው የቀሩ ብዙ ሰዎች እንዳሉም ይታወቃል።
 
ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ “ከቻለችው ምን ችግር አለው? ዋናው መስራቷ ነው” የሚሉት አስተያየቶች ናቸው፣ ሌላ ትኩረቴን የሳቡት።
 
ታዲያ ትናንትና “የትግራይ የበላይነት ነገሰ” ያልነው ለምን ነበር?
 
አንድ መስሪያ ቤት ውስጥ ከጥበቃ እስከ ሀላፊ ድረስ ትግሬዎች ናቸው የሚቀጠሩት እና ቦታ ቦታ የያዙት የተባለው ለምንድን ነው?
 
ኮንዶሚነም ቤት እስከከፈሉ ድረስ ቢሰጣቸው ምን ችግር ነበረው?
 
የጥበቃ ሰራተኛው እስከጠበቀ ድረስ ትግሬ ሆነ ምን ሆነ ለምን ደነቀን?
 
የመከላከያ ሰራዊቱ ብሔር ስብጥር ለምን አሳሰበን?
 
የአውሮፕላን አስተናጋጇ እስካስተናገደች እና አውሮፕላኑ ስራ እስካላቆመ ድረስ፣ ትግሬ ሆነች ምን ሆነች ምን አገባን?
 
መርካቶ ንግዱ እስካልታጎለ ድረስ፣ ጉራጌዎችን አፈናቅለው በግብር እና በኮንትሮባንድ ደግፈው ትግሬዎችን ቢያስፋፉ ምን አስጨነቀን?
 
የተለያዩ ሀላፊነት ቦታዎች ላይ የተሾሙትስ አለመቻላቸው በምን ታወቀና ነው ትግሬ መሆናቸው ያስከፋን?
 
ታዲያ ድካማችን ሁሉ ለምን ነበር?
 
አገሪቱ ላይ ሁሉም ዜጋ እኩል ተጠቃሚ ይሁን ከሚል ቅንነት አይደለምን? ፍትህ እና ተጠያቂነት እንዲነግሱ፣ የዘመድ እና የካድሬ አሰራር እንዲወገድ አይደለምን?
 
“አዲስ ንጉስ እንጂ ለውጥ መቼ መጣ” የሚለው ሙዚቃ ትዝታ ይሁንልን! የትናንቱን የጠላነውን፣ በአዲስ ዛሬ ለመተካት አይደለም ተስፋ እና ጉጉቱ!
 
ኢፍትሀዊ አሰራር ይውደም!

ሲደፈርስ!

ትግሉ መስመር እስኪይዝ ድረስ፥ እንኳን በኢትዮጵያ አንድነት ከሚያምኑ ኦሮሞዎች ጋር መስማማት ቀርቶ፥ የአማራ እና የኦሮሞ ዛፍነትና የስሮቻቸው ተጨባባጭነትም ይቀነቀናል። እስከዚያ፥ ተመልካች (audience) እየለዩ፥ ዓላማን ለመሸፋፈን እና ወቅታዊ ተቀባይነትን ለማግኘት፥ በየቋንቋው የተለያየ ነገር ያስተላልፋሉ። ስጋቱን ለመግለጽ የሚሞክር ቢኖር፥ በ“ትግል አታዳክም” ታፔላ ሊሸማቀቅ ይዳከራል። ትግሉ መስመሩ ተጠናክሮ ዳር ሊይዝ አጥቢያው ሲመስል ደግሞ፥ “አገር ይፍረስ! እንክትክቱ ይውጣ!” ይባላል።
 
ይገርመኛል! ፊደል መቁጠር ለዚህ ለዚህ ካልጠቀመ ለምን ሊጠቅም ነው? በተለይ በባዕድ አገር ላይ፥ “ከየት ነህ? ማን ነህ? ምን ቋንቋ ትናገራለህ? ለምን መጣህ?” ሳይባል፣ ተመቻችቶለት እንደልቡ እየኖረ እና እንደ ኅብረተሰቡ አካል ተመሳስሎ እየተማረ፣ በሞያው እያገለገለ፣ መብቱን አስከብሮ ሸጦ ለውጦ እየተዳደረ፣ ቢሻው ሀብት ንብረት እያፈራ እና ቋሚ እሴት እያጠራቀመ፥ እንዴት ለገዛ ወገኑ እልቂት መፈራረስን ይመኛል? በእንግድነት በተድላ ከሚኖርበት ቦታ እንኳን እንዴት ይህንን ትምህርት አልቀሰመም? እንዴት በመከራ ውስጥ ሆኖ ነጻነቱን ሲፈልግ፥ ባልጠገበ አንጀቱ በአምባገነን ስርዓት ወድቆ የቀረ ወገኑ ደም ላይ ይሳለቃል?
 
ይኽስ ማንን ይጠቅማል? ሰድቦ ለሰዳቢ አሳልፎ ለመስጠት ካልሆነ፥ ማንን ወደፊት ያራምዳል? እስከመቼስ በአንድነት እና በትብብር አብሮ የሚኖረው ሕዝብ፣ በሆዳም ‘አዋቂ’ ነን ባይ ፖለቲከኞች “አይ አብረህ መኖር አትችልም” ይባልለታል? ለእነሱ አገር በማፍረስ ዋጋም ቢሆን የሚገኝ የስልጣን ጥማት ማርኪያነት ለምን ይናፈቃል? ትናንት የመጡትስ ከዚህ መች ተለይተው ጀመሩት? ደግሞ፥ “ይሁን” ቢባልና ቢሳካስ በሰላም መኖር ይቻል ይመስላቸዋል? ወይስ በቃ አገሪቱን ተቃርጠው በየክልሉ ተመሳፍነው ሊያስገብሩ ነው?
 
እንዲህ ዓይነቱ ጨዋታ፥ የሴረኞችን ህልም ከማሳካት ይልቅ፥ ሙሉ አገሩ ስለአንድነቱ በጋራ እንዲቆም እንደተላለፈ ጥሪ የሚቆጠር ነው። አገራችን በጨካኝ ስርዓት እጅ ባለችበት በዚህ ሰዓት፥ ‘አገር አፍራሽ ሆነን፣ ልንበትንህ መጥተናል። እኛ መሲህ ነን’ ዓይነት ነጋሪት ብትጎስሙበትና ከያዘው ትግል ልታጓትቱት ብትጥሩ፥ አይምራችሁ! የነጭ ስልጣኔ፣ ገንዘብና የተሻለ ኑሮ ሳያጓጓቸው በባዶ እግር እና በጨበጣ ውጊያ ጣሊያንን እንኳን ገርፎ የመለሰ ሕዝብ አገር ሰዎች ነንና መቼም አይሳካላችሁም!
 
መተዋወቅ ያስፈልጋል። ስለማታውቁት፣ ወይም ድሮ አውቃችሁት ስለረሳችሁት ሕዝብ ነው የምትደሰኩሩት። “ዶሮ ብታልም ጥሬዋን” እንዲሉ፥ መከራ የፈነቀለውን እና በጋራ የቆመውን ሕዝብ “የኔ ጦር ነው…የኔ” ትባባሉበታላችሁ። ቢቆስል፥ ‘የውሻ ቁስል ያድርግልህ’ ያላላችሁትን፣ ቢሞትበት፥ የቤተሰቡን ትኩስ አስከሬን ፎቶ በየገጹ ከመቀባበል ያላላፈ፥ ጠንከር ያለ “ነፍስ ይማር” እንኳን ያላላችሁለትን፥ ደሙን ገብሮ ነጻነቱን ለመቀዳጀት ደፋ ቀና ሲል… ‘እኛ ነበርን እግዚአብሔሮችህ፣ ከኋላህ ቆመን በለው በለው ስንልህ የነበርን። አሁን ድል አገናኝቶን የባንዲራህን ጨርቅ አስቀድደን፣ ልንሰቅልልህና ልናሸጋግርህ መጥተናል’ ብትሉት አይሰማችሁም። ኢህአዴግም በብዙ ነገር ከፋፍሎ፣ በትንሽ ትንሹ ጠርንፎ፣ በሀውልትና በፕሮፖጋንዳ፣ ‘በታትኜ ያዝኩት’ ያለው ሕዝብ፥ አንድ ሆኖ እያስደነበረው ነው።
 
አሰቃቂው የኢሬቻ እልቂት ሳይቀር እንኳን፥ እንደጥሩ ትግል ማቀጣጠያ ቤንዚንነት ያስደሰታችሁና፣ እንደ ጥብስ ወሬ ያነቃቃችሁ፥ “የአገር መፍረስ ህልመኞች” እንዳላችሁ ልባችሁ የሚያውቅ ታውቁታላችሁ። ቱኒዚያ ቦአዚዝ ራሱን ቢለኩስ፥ ቤንዚን ሆኖ የነጻነት መንገድ እንደጠረገላቸው፣ ለግብጽ አብዮትም የካሊድ ሰይድ ግፈኛ አገዳደል እርሾ ሆኖ እንዳሰባሰባቸው፥ ሰው በሞተ ቁጥር ህልማችሁን የማሳካት ሴራችሁ ከግብ እንደተቃረበ በመቁጠር ብቻ… በመሰባሰብ ፈንታ፣ ‘የድል ዋዜማ ላይ ነንና ብቻችንን እንቁም’ በሚል ብልጣብልጥነት ስንቱን ለማግለል እንደጣራችሁም፣ ስንቴ በጠላት እንዳሳለቃችሁብን የምታውቁ ታውቁታላችሁ። ኦሮሞ ያልሆነ ሰው የኦሮሞ ፖለቲካ ላይ ሀሳብ ቢሰጥ፥ በ’oromophobia’ ፈርጃችሁት፣ ፍርሀትን ለመትከል የለፋችሁም ታውቁታላችሁ።
 
“እንለይህ” የምትሉት ወገን፥ በጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ እንኳን አንድ ቦታ የተከማቸ፣ ባህሉንም ያልተወራረሰ አይደለም። እንለይህ የምትሉት ወገን፥ እንጀራ ተበዳድሮ እና ሚጥሚጣ ተዋውሶ፣ ለቡና እየተጠራራ፣ ልጁን እርስ በርስ እየተቀጣጣ፣ ቤቱን ቁልፍ አልባ ትቶት “መጣሁ” ተባብሎ የኖረ ነው። ጡት ሳይቀር ተጋርቶ ያደገው ሕጻን ብዙ ነው። በከተሞች ብልጭ ድርግም ባይ መብራቶች የተጋረደ ብዙ ያልታየ ሕዝብ አለ። በአካባቢ መቀየር እንኳን የኑሮ ቀውስ የሚገጥመው ሕዝብ ነው።
 
“ጠላቶችህ ናቸው” ብላችሁ ስለወዳጆቹ ክፉ ለመንገር የምትደክሙለት ሕዝብ ያን ያህልም ክፉና ደግ የማይለይ እንዳልሆነ እንኳን አትገነዘቡም። ንቃችሁት ተነስታችሁ ነው እናስከብርህ የምትሉት። ከዚህ በላይ ‘እየታገልኩልህ ነው’ የሚሉትን አለማወቅ የለም!
 
የወገኖቻችን ደም በከንቱ ፈሶ አይቀርም!
 
ይጮሃል! ሁሌም ይጮኻል! ከጩኸቶቹ ሁሉም የጎላና የከበደ የሚሆነው፥ ‘ምሁራን’ ተሰብስበው ደሙን ሊያቃልሉበትና፣ ለጠላቶቹ መስዋዕት ሊገብሩበት እንደሆነ ያወቀ ጊዜ ሳይሆን አይቀርም።
 
የደፈረሰው ጠርቶ፣ የተከፈለው መስዋዕት እንደሚያጠባብቀንና ልቦቻችንን አክሞ በጋራ እንደሚያኖረን፣ አገሪቱንም ለሰው ልጆች ሁሉ የሚመች ስርዓት የሰፈነባት እንደሚያደርግ አልማለሁ!
 
ከዛሬ ነገ ይሻላል!
 
#Ethiopia

መጽሐፍት ሲያዞሩ…

n1704ፀሐፊውን… የቻሉትን አሰሩ፣ የቻሉትን አባረሩ፣ የቻሉትን ደግሞ ለማስፈራራት ላይ ታች አሉ። የቻሉትን የሚፈልጉትን እንዲጽፍ አድርገው እቅፍ ድግፍ አድርገው ያዙት።
 
የመጽሐፍትን መታተም ለማስታጎልና የፀሐፊዎችን ቅስም ለመስበር፥ የመጽሐፍት ህትመት ዋጋን በወረቀት እና በሰበብ አስባብኩ ከፍ አደረጉት።
 
ነባር መጽሐፍትን በጨረታ እስከመሸጥ ድረስ፥ የአገራዊና ወቅታዊ ጉዳዮች መጽሐፍትን ድራሽ ለማጥፋት የሚችሉትን ሁሉ አደረጉ። ከነሱ ሀሳብ የተለየው ላይ ሁሉ ጥርሳቸውን ነከሱበት።
 
“ለሽብር የሚያነሳሱ መጽሐፍት” ብለው በራሳቸው ጊዜ ተሸብረው፣ ሕብረተሰቡ እንዲሸበር እና ተሸማቆ እንዲኖር፣ ሲያነብም እንዲሳቀቅ አዋጅ አንጋጉ።
 
ይኸው ደግሞ፥ መጽሐፍ አዙረው እውቀትን በማስፋፋትና ራሳቸውን በመደጎም የሥራ መስክ ላይ የተሰማሩ ምስኪን መጽሐፍት አዟሪዎችን ማሰር ጀመሩ።
 
የሪፖርተር ጋዜጣ ዜና እንዲህ ይነበባል….

አመፅ ቀስቃሽ ናቸው የተባሉ መጻሕፍት በመሸጥ የተጠረጠሩ አዟሪዎች ታሰሩ

ኅብረተሰቡን ለአመፅ የሚገፋፉና ግጭት ሊፈጥሩ የሚችሉ መጻሕፍት በማዘዋወርና በመሸጥ የተጠረጠሩ መጽሐፍት አዟሪዎች፣ ከነሐሴ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ መታሰራቸው ታወቀ፡፡

ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ መጻሕፍት አዟሪዎች በተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎች መታሰራቸውንና በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ተረኛ ችሎት ቀርበው ጊዜ ቀጠሮ እንደተጠየቀባቸው ቤተሰቦቻቸው ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

አዟሪዎቹ የተጠረጠሩት ሕዝብ የሚያነሳሱና አመፅ የሚቀሰቅሱ መጣጥፎችን በፍትሕ ጋዜጣ ላይ በማተም ክስ ተመሥርቶበት የሦስት ዓመታት ጽኑ እስራት የተፈረደበት ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፣ በቅርቡ ‹‹የፈራ ይመለስ›› በሚል ርዕስ ያሳተመውን መጽሐፍ፣ ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ ‹‹የኦሮሞና አማራ የዘር ግንድ›› በሚል ርዕስ ያሳተሙት መጽሐፍና ጋዜጠኛ ሙሉ ቀን ተስፋው ‹‹የዘመኑ ጥፋት›› በሚል ርዕስ ያሳተመውን መጽሐፍ በማዞር ሲሸጡ ስለተገኙ መሆኑ ተገልጿል፡፡

ጋዜጠኛ ተመስገን ቀደም ብሎ ክስ ተመሥርቶበትና ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ቅጣት የተጣለበትን መጣጥፍና በድጋሚ በመጽሐፍ መልክ ያሳተመውን መጽሐፍ ማሠራጨት ወንጀል መሆኑን ፖሊስ ለፍርድ ቤት ማስረዳቱ ታውቋል፡፡ ሌሎቹም የተጠቀሱት መጻሕፍት አመፅ ቀስቃሽ መሆናቸውን በመግለጽ መሠራጨታቸው ተገቢ አለመሆኑን ፖሊስ ለፍርድ ቤት አስረድቶ፣ መጻሕፍቱ ሲታተሙ ያተማቸው ማተሚያ ቤት በመጽሐፉ ላይ መግለጽ የነበረባቸው ቢሆንም ሳይገልጹ መቅረታቸውንም አክሏል፡፡ ይኼም ሆን ተብሎ መንግሥት ቁጥጥር እንዳያደርግ በድብቅ የሚሠራ ሕገወጥ ተግባር መሆኑን በማስረዳት፣ ለተጨማሪ ምርመራ ተጨማሪ ጊዜ መጠየቁ ተገልጿል፡፡

የተወሰኑ አዟሪዎች መጻሕፍቶች ተነጥቀው ሁለተኛ እንዳያዞሩ ፈርመው መለቀቃቸውንና ማተሚያ ቤቱን እንዲጠቁሙ ተገደው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ሐሙስ ነሐሴ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበው ጊዜ ቀጠሮ የተጠየቀባቸው መጻሕፍት አዟሪዎች ሰኞ ነሐሴ 23 ቀን 2008 ዓ.ም. በድጋሚ ፍርድ ቤት እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡

አሜሪካ ድምጽ ሬድዮም ቀድሞ እንዲህ ዘግቦት ነበር…

መጽሐፍ አዟሪዎቹ በተለይ የተመስገን ደሳለኝ፣ የሙሉጌታ ሉሌና የዶ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ መጽሐፍ መሸጥ እንዳልቻሉ እነዚህን መጽሐፍትና ሌሎች የታሪክና የፖለቲካ መጽሐፍት ይዘው ሲገኙ እንደሚደበደቡ፣ እንደሚታሠሩና አንዳንዴም ለመለቀቅ ከደንብ አስከባሪዎች ጉቦ እንደሚጠየቁ ተናገሩ።

‘መጽሐፍቱን ማዞር ወንጀል ቢሆን’ እንኳን፥ በጎልማሶች ት/ት (መሰረተ ትምህርት adult education) ፕሮግራም እንኳን ማንበብና መጻፍ ያላስተማሩትን ዜጋ ምን ብለው “አመጽ ቀስቃሽ” መጽሐፍ ይዘህ ዞረኻል ብለው ያስሩታል? ያዋክቡታል? ይቀጡታል?
“አህያውን ፈርቶ ዳውላውን” አሉ። ከቻሉ ሀሳብን ማሰሩን አይሞክሩትም ነበር?!